በአዲስ መልክ የተደራጀው የደቡብ ኦሞ ዞን አመራሮች ከመቼውም ጊዜ በላይ ለዞኑ ህዝብ ለውጥ ትኩረት ሰጥተው እንደሚሠሩ ገለፁ

በአዲስ መልክ የተደራጀው የደቡብ ኦሞ ዞን አመራሮች ከመቼውም ጊዜ በላይ ለዞኑ ህዝብ ለውጥ ትኩረት ሰጥተው እንደሚሠሩ ገለፁ

ሀዋሳ፡ መስከረም 07/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በአዲስ መልክ የተደራጀው ደቡብ ኦሞ ዞን ኃላፊነት የተሰጣቸው አመራሮች ከመቼውም ጊዜ በላይ ለዞኑ ህዝብ ለውጥ ልዩ ትኩረት ሰጥተው እንደሚሠሩ ገለፁ።

የዞኑ አመራር በቀጣይ ወደ ሥራ መግባትና የማህብረሰቡ ውዝፍ ልማታዊ ጥያቄዎችን ደረጃ በደረጃ መፍታት በሚያስችል ሁኔታ ላይ የጋራ ውይይት አድርጓል።

ከዚህ በፊት በአደረጃጀትና በተለያየ ምክንያት በየአካባቢው ልማታዊ ሥራዎች በተፈለገው ልክ እየለሙ ባለመሆኑ፥ በአሁኑ ወቅት በአዲስ መልክ በተደራጀው ደቡብ ኦሞ ዞን ኃላፊነት የተሰጣቸው አመራሮች ለህዝቡ ለውጥ ተግተው እንደሚሠሩ ገልፀዋል።

ዞኑ የውስጥ ገቢን ለማሰባሰብ የሚያስችሉ አጋጣሚዎች መኖራቸውን ጠቁመው፥ ይህንን በተሻለ መልኩ ስኬታማ በማድረግ ወደ ልማት ለመቀየር ይሠራል ብለዋል።

በደቡብ ኦሞ ዞን ያሉ 15 ብሔር ብሔረሰቦች አንድነትና ሰላም ከመቼውም ጊዜ በላይ ተረጋግጦ የመልማት ፍላጎት እንዲሳካ ልዩ ጥረት እንደሚደረግም ገልፀዋል።

የደቡብ ኦሞ ዞን የመንግሥት ዋና ተጠሪ እና ብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ ብርሃኑ አረጋ እንደገለፁት በአዲስ መልክ በተደራጀው ደቡብ ኦሞ ዞን ሀላፊነት የተሰጣቸው አመራሮች በአጭር ጊዜ ወደ ሥራ በመግባት ህዝቡን ማገልገል እንዳለባቸው አሳስበዋል ።

የአመራሩ ምደባና ሹመት በግልፀኝነት መሠራቱንም ገልጸዋል።

በምክትል ዋና አስተዳዳሪ ማዕረግ የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማልኮ በበኩላቸው፥ አዲስ የተደራጀው ደቡብ ኦሞ ዞን የህዝቡ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በመሆኑ በዚህ ልክ ይሠራል ብለዋል።

አንድነት በዓለም ላይ ልዩ የጥንካሬ መገለጫ በመሆኑ የአመራሩንና የህዝቡን አንድነት ኢትዮጵያዊነትን በሚገልፅ መልኩ በማስጠበቅ የተሻለ ኢኮኖሚና ለውጥ የሚመዘገብበት ዞን እንዲሆን በትኩረት እንደሚሠራ አቶ ማዕከል አብራርተዋል ።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን