በቤንች ሸኮ ዞን አዲስ አመት ምክንያት በማድረግ ለአቅመ ደካሞችና ለተማሪዎች ድጋፍ ተደረገ

ሀዋሳ፡ ጳጉሜ 06/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) ድጋፉን ያደረገው የሴቶች ህፃናትና ማህበራዊ ጉዳይ መምሪያ ከዞኑ ወጣቶች ማህበር ጋር በመቀናጀት የተካሄደ መሆኑን አመላክተዋል፡፡

የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ቀበሌ መንገሻ በስነ-ስርዓቱ ላይ ተገኝተው በሚዛን አማን ከተማ ለሚገኙ አቅመ ደካሞችና ለተቸገሩ ወገኖች የድጋፍ ስጦታውን አበርክተዋል።

ዋና አስተዳዳሪው ለተቸገሩ ተማሪዎችና ቤተሰቦቻቸው ደብተርና እስክሪፕቶ ድጋፍ ያደረጉ ሲሆን መጪው ዘመን የሰላም፣ የጤናና የብልጽግና እንዲሆንላቸው መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።

የቤንች ሸኮ ዞን ሴቶች፣ ህጻናትና ማህበራዊ ጉዳይ መምሪያ ኃላፊ ወይዘሮ ውቢት ገምታ እንደተናገሩት፥ አዲሱን አመት ምክንያት በማድረግ ካለን ላይ ቀንሰን አቅመ ደካሞች በዓሉን በደስታ እንዲያሳልፉ ታስቦ 50ሺህ ብር የሚያወጡ የበዓል የፍጆታ ዕቃዎችና ለተማሪዎች የሚሆኑ የትምህርት ቁሳቁሶች ናቸው ብለዋል፡፡

ድጋፉ ዘይት፣ ዳቦ ዱቄት ለተቸገሩ ወገኖች ድጋፍ የተደረገ ሲሆን ለ20 የአቅመ ደካማ ተማሪዎች 20 ደርዘን ደብተርና 100 ፍሬ እስክሪፕቶ ድጋፍ መደረጉን ተናግረዋል።

የቤንች ሸኮ ዞን ወጣቶች ማህበር ሰብሳቢና የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ቅ/ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ መንግስቱ ኃይሌ እንደገለጸው ወጣቱ ትውልድ ካለው ላይ በማካፈል የተቸገሩና አቅም የሌላቸውን ወገኖች በመርዳት ማህበራዊ ኃላፊነቱን ሊወጣ ይገባል ብለዋል።

በእለቱ ድጋፉ የተደረገላቸው ወገኖችም የዞኑ መንግስት በዓሉን ምክንያት በማድረግ ላደረገላቸው ድጋፍ አመስግነው በበዓል ስጦታው መደሰታቸውን ገልፀዋል።

ዘጋቢ፡ ጦያር ይማም – ከሚዛን ቅርንጫፍ