ህብረተሰቡ ሀሰተኛ ገንዘብ አትመው በማሰራጨት ለሌብነት ከተሰማሩ አታላዮች እና ከፎርጅድ ብር ራሱን መጠበቅ  እንዳለበት ተጠቆመ

ህብረተሰቡ ሀሰተኛ ገንዘብ አትመው በማሰራጨት ለሌብነት ከተሰማሩ አታላዮች እና ከፎርጅድ ብር ራሱን መጠበቅ  እንዳለበት ተጠቆመ

ሀዋሳ፡ ጳጉሜ 04/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) ህብረተሰቡ ሀሰተኛ ገንዘብ አትመው በማሰራጨት ለሌብነት ከተሰማሩ አታላዮች እና ከፎርጅድ ብር ራሱን መጠበቅ  እንዳለበት የሀዲያ ዞን ፓሊስ መምሪያ አስታወቀ።

መምሪያው የዘመን መለወጫ በዓልን ምክንያት በማድረግ ወንጀሎች እንዳይበራከቱ ለመከላከል ቅድመ ዝግጅት ማጠናቀቁን አስታወቀዋል።

በመምሪያው የወንጀል መከላከል ዲቪዥን ኃላፊ ኮማንደር ሳህሉ ሀይሌ ህብረተሰቡ በሰላም ወጥቶ እንዲገባ ሰላምና ፀጥታ ማስከበር የፖሊስ የዕለተ ዕለት ተግባር ቢሆንም በዓላት ላይ ወንጀሎች ስለሚበረከቱ ልዩ ትኩረት እንደሚሰጥ ተናግረዋል።

የዞኑ ፖሊስ መምሪያም ይህንኑ ተግባር ለመወጣት ከሌሎች የፀጥታ አካላትና ከበጎ ፈቃደኛ ወጣቶች ጋር በመቀናጀት ሕብረተሰቡ የዘመን መለወጫንም ሆነ ያሆዴን በሰላም እንዲያሳልፍ ለማስቻል ወደ ተግባር መግባቱን በመጠቆም።

ቅንጅታዊ እንቅስቃሴ ከተጀመረ ወዲህ በ30 ሺህ ብር በሬ ለሸጠው አርሶ አደር 18 ሺህ የሀሰተኛ ብር ቀላቅሎ የሰጠውን ተጠርጣሪ ይዞ ምርመራ ከማጣራት ጀምሮ በርካታ ሌቦችን በገበያ አካባቢዎችና በማታ ጨለማን ተገን በማድረግ የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦችን በቁጥጥር  ስር እየተደረገ መሆኑን ኮማንደር ሳህሉ አክለዋል።

ሞባይል ባንኪንግ የሚጠቀሙ ዜጎችን ሎተሪ አሊያም ይሸለሙ ይጠቀሙ ዕድል እንደደረሳቸው እንዲሁም ከውጭ አገራት ገንዘብ እንደተላከላቸው በመንገር ምስጢር ቁጥር ጠይቆ አካውንት ላይ ያለውን ብር አንድም ሳያስቀሩ መውሰድ እየተባባሰ የመጣ የወንጀል ዓይነት እንደሆነ የገለጹት ሀላፊው ባለፉት አራት ቀናት ውስጥ ብቻ ከአምስት የሚበልጡ የዞኑ ነዋሪዎች በዚህ መንገድ ገንዘብ መዘረፋቸውን ጠቁመዋል ነው ያሉት።

ህብረተሰቡ ለበዓላት ከውጭ አገራት የሚላኩ ገንዘቦችን መሰል ወንጀሎች በማይፈጸምበት መልኩ መጠቀም እንዳለበት መልዕክት ያስተላለፉት ኮማንደሩ አጠራጣሪ ሁኔታዎች ሲያገጥም በአቅራቢያ ለሚገኝ ፖሊስ  ፈጥኖ እንዲያሳውቅ ጠይቀዋል።

ዘጋቢ: ጌታቸው መጮሮ – ከሆሳዕና ጣቢያችን