የአገልጋይነት ቀን በሆሳዕና ከተማ እየተከበረ ነው

ሀዋሳ: ጳጉሜ 01 /2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሀዲያ ዞን የአገልጋይነት ቀን እየተከበረ ነው፡፡

የአገልጋይነት ቀን በሀዲያ ዞን ሆሳዕና ከተማ በተለያየ ዝግጅት እየተከበረ ሲሆን እለቱን አስመልክተው በጤና ተቋማት እየተሰጠ ያለውን አገልግሎት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብርሀም መጫ ተመልክተዋል::

ሀገራችንን ከልብ በቀናነት የምናገለግልበት ቀን ነው ያሉት ዋና አስተዳዳሪው እርካታችንም የተገልጋዩ እርካታ ላይ የሚመሰረት ነው ብለዋል::

የአገልጋይነት ቀን መከበሩ ታታሪዎችን ይበልጥ የሚያነሳሳ እና ለሌሎችም አርዓያ በመሆን ለሀገር የተሻለ ሥራ ለማበርከት ያስችላል ብለዋል::

እለቱ ትልቅ ዓላማ ያነገበ በመሆኑ ለተያዘው ሀገራዊ ለውጥ ሁሉም የሚጠበቅበትን እንዲያበረክት ጥሪ አቅርበዋል::

እነዚህ የጳጉሜ ቀናት የሚያስተላልፉትን መልዕክት ሚዲያው በሚገባ ለህዝብ በማድረስ አዎንታዊ አስተዋጽዖ ሊያበረክት እንደሚገባ የገለፁት ደግሞ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ አምሪያ ሲራጅ ናቸው::

አገልግሎት መስጠት የአንድ ቀን ተግባር ብቻ ባለመሆኑ ዘወትር ትጋትና ታታሪነት መላበስ እንደሚገባም አስገንዝበዋል::

በሀገር አቀፍ ደረጃ በተለያዩ ስያሜዎች የሚከበሩ የጳጉሜ ቀናት በተመሳሳይ በክልሉ በተጠናከረ መልኩ ይከበራል ብለዋል::

ዘጋቢ: ማሬ ቃጦ