ሀዋሳ፡ ጳጉሜን 01/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) የዳውሮ ዞን ዋና አስተዳደሪ አቶ ደስታ ደምሴ ለዳውሮ ብሔረሰብ ዘመን መለወጫ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
የ”ቶክ-በኣ” በኣል በዳውሮ ብሔረሰብ ዘንድ ከጥንት ጀምሮ ተያይዞ የመጣ የዘመን መለወጫ ሲሆን አመቱን ሙሉ ወጥቶ ወርዶ የተሻለ በማምረት በአዲስ አመት ዋዜማ ሰውም ሆነ የቤት እንስሳት ጠግበው እንዲያድሩና ቤት ውስጥ ያሉ የሽክላ እቃዎች በውሃ ተሞልተውና ተከድነው እንዲቀመጡ የሚያስተምር ነው በማለት የዳውሮ ዞን ዋና አስተዳደሪ አቶ ደስታ ደምሴ ገልጸዋል።
በዕለቱ በአሮጌው አመት የነበረ መጥፎ ነገር ሁሉ ወደ አዲሱ ዓመት እንዳይሻገር ሽማግሌዎች ፀሎት የሚያደርጉበትም ነው ብለዋል።
የጨረቃ እንቅስቃሴን መሰረት በማድረግ የሚከበረው የዳውሮ ብሔረሰብ ዘመን የመቁጠርና ወቅቶችንም የመለየት እውቀት የበለጠ ለምቶና ተጠንቶ ለሀገር እሴትነት ሊውል የሚገባ መሆኑንም አመላክተዋል።
የዳውሮ ብሔረሰብ ዘመን መለወጫ በዓል ለዞኑ ማህበረሰብና እንደሀገርም የሚሆኑ በርካታ እሴቶች ያሉት በመሆኑ ይህን በዓል አጠናክሮ ለማስቀጠል የዞኑ አስተዳደርም ከፍተኛ ትኩረት መስጠቱን አስረድተዋል።
በበዓሉ እለት የቀጣይ አመቱን የሥራ ተግባራትን በሚመለከት የአባቶች ምክር፣ ለአካባቢው እና ሀገር ፀሎት የሚደረግበትና የብሔረሰቡ ባህላዊና ታሪካዊ ቅርሶችንም ለማስተዋወቅ እድል የሚፈጥርበት መሆኑን ዋና አስተዳደሩ ተናግረዋል።
በዓሉ የህዝብ መሠረት ያለው በመሆኑ ይህንን በማጥናት፣ በማሳወቅና ለትልድ ለማሸጋገር የዘርፉ ተቋማት የበኩላቸውን ተግባር አጠናክረው መቀጠል እንደሚገባቸው አንስተዋል።
የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ደስታ ደምሴ እንኳን ለዳውሮ ብሔረሰብ ዘመን መለወጫ ቶክበኣ በዓል በሠላም አደረሳችሁ በማለት አዲሱ ዓመት የሥራ፣ የበረከት፣ የመተባበር ፣ የሠላምና የብልጽግና እንዲሆንም ተመኝተዋል።
ዘጋቢ፡ ዮሐንስ መካሻ – ከዋካ ጣቢያችን

More Stories
ህዝበ ሙስሊሙ የመውሊድ በዓልን ሲያከብር በብዝሃነት ውስጥ የሚንፀባረቁ የመረዳዳትና የአብሮነት በጎ እሴቶችን ይበልጥ በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ ተገለጸ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ኃላፊና የየዞን ከፍተኛ አመራሮች በሣውላ ማረሚያ ተቋም አረንጓዴ አሻራቸውን በማኖር ልዩ ልዩ የልማት ሥራዎችን ጎበኙ
በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ምርመራ እና ልየታ ተካሄደ