በጋሞ ዞን አርባ ምንጭ ከተማ በሻራ ቀበሌ የሠላም መደፍረስ ወደነበረበት መመለሱን የአካባቢው ነዋሪዎች አስታወቁ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 26/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሻራ ቀበሌ ቀደም ሲል በአርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ ስር የነበረ ቢሆንም የዞኑ መንግስት ከቀበሌው ነዋሪዎች ጋር ባደረገው ተከታታይ ውይይት ወደ አርባምንጭ ከተማ እንዲቀላቀል በመወሰኑ መደሰታቸውን የሚናገሩት ነዋሪዎቹ የአካባቢው ህዝብ መሰረታዊ የልማት ፍላጎቱ ምላሽ የሚያገኝበት ነውም ብለዋል፡፡

የሻራ ቀበሌ ቀደም ሲል በአርባምንጭ ዙሪያ ወረዳ በነበረበት ወቅት የህዝብን መሬት ለግል ጥቅማቸው ያዋሉትን የቀበሌው አመራሮችና ግለሰቦች በህግ ጉዳያቸዉ እየታየ መሆኑን የአርባምንጭ ከተማ ሠላምና ፀጥታ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ገበየሁ ፃራ ገልፀዋል።

ችግሩ እንዳይባባስ በተለያዩ መንገዶች ለማግባባት ጥረት ተደርጓል የሚሉት የጋሞ ዞን ሠላምና ፀጥታ መምሪያ ኃላፊ አቶ ወንድሙ ኩንሳ በአካባቢው በጥቂት ኃይሎች የሚፈፀመውን የሰብአዊ ጥሰት ለመከላከል የፀጥታ ኃይሉ የህግ ማስከበር ተግባሩን ሀላፊነት በተሞላ ሁኔታ መወጣቱን ገልፀዋል።

ህግ ለማስከበር በተደረገዉ ጥረት በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱን እና የሰዎች ህይወት ማለፉን ተናግረዋል፡፡

ከጉዳዩ ጋር ግንኙነት ያላቸዉ ግለሰቦች በህግ ቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው እየተጣራ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡

አከባቢው ዘላቂ ሠላም ይኖረው ዘንድ ትኩረት ተሰጥቶት ይሰራልም ተብሏል፡፡

ዘጋቢ፡ በኃይሉ ሙሉጌታ – ከአርባ ምንጭ ጣቢያችን