በዘንድሮው የማህበራዊ ሳይንስ ፈተና በሁሉም አከባቢዎች በሰላም እንደተጠናቀቀና የተሻለ ውጤት የሚጠበቅ መሆኑን ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ገለፁ

በዘንድሮው የማህበራዊ ሳይንስ ፈተና በሁሉም አከባቢዎች በሰላም እንደተጠናቀቀና የተሻለ ውጤት የሚጠበቅ መሆኑን ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ገለፁ

ሀዋሳ፡ ሐምሌ 21/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) በዘንድሮው የማህበራዊ ሳይንስ ፈተና በሁሉም አከባቢዎች በሰላም መጠናቀቁንና የተሻለ ወጤት የሚጠበቅ መሆኑን የኢፌዴሪ ትምህርት ሚኒስትር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ በሳውላ ካምፓስ ተገኝተው ገልፀዋል፡፡

ከ500ሺህ በላይ የማህበራዊ ሳይንስ ተፈታኝ ተማሪዎች ፈተናቸውን በተሳካ ሁኔታ ማጠናቀቃቸውንም ተናግረዋል፡፡

የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ በምክትል ፕሬዚዳንት ማዕረግ የሣውላ ካምፓስ ኃላፊ አቶ ገብረመድን ጫሜኖ እንደገለጹት፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚሰጠውን የማህበራዊ ሳይንስ ፈተና በሳውላ ካምፓስ ከ2ሺህ በላይ የሚሆኑ ተማሪዎች ተቀብሎ በተሳካ ሁኔታ ተጠናቋል።

ፈተናው በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ መሰጠቱ ኩረጃና ሰርቆትን ለመከላከል ወሳኝነት እንዳለው በሣውላ ካምፓስ ፈተናውን ያጠናቀቁ ተማሪዎች በሰጡት አስተያየት ገልፀዋል፡፡

አክለውም ፈተናው በተማሩት ልክ  በመቅረቡ የተሻለ ውጤት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል።

በመርሃ-ግብሩ ላይ የኢፌዴሪ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ፣ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚንስትር አቶ ተስፋዬ በልጅጌ ጨምሮ ሌሎች የፌደራልና የክልል ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች በአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ ሳውላ ካምፓስ ተፈታኝ ተማሪዎች ጎብኘተው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መረሃ-ግብር  አካሂደዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ስንታየሁ ሙላቱ – ከሳውላ ጣቢያችን