ሞዴል የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን መሠረተ ልማት ማሟላትና ምቹ የመማሪያ ከባቢን ለልጆች መፍጠር ለቀጣዩ የትምህርት ደረጃዎች መሠረት መሆኑ ተገለጸ

ሞዴል የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን መሠረተ ልማት ማሟላትና ምቹ የመማሪያ ከባቢን ለልጆች መፍጠር ለቀጣዩ የትምህርት ደረጃዎች መሠረት መሆኑ ተገለጸ

በዳውሮ ዞን ማራቃ ወረዳ ትምህርት ለትውልድ ኢኒሼቲቭ አካል የሆነው ሞዴል የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በዛሬው ዕለት ተመርቋል፡፡

የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ አቶ አክሊሉ አሰፋው፤ ሞደል የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በሥነ-ምግባር የታነጸ ሀገር ተረካቢ ትውልድ የሚቀረጽበት ነው ብለዋል።

በተለይም ባለፉት የለውጥ ዓመታት “ትምህርት ለትውልድ” በሚል መሪ ሀሳብ የተጀመረው ንቅናቄ የሚታይ ውጤት እንደተመዘገበበት አረጋግጠዋል።

የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ትምህርት ቢሮ ምክትል ኃላፊና የመምህራን ልማት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ማርቆስ ቡልቻ በበኩላቸው፤ መንግስት የትምህርት ስብራትን ለመጠገን የሚያስችሉ የተለያዩ ፖሊሲዎችን ቀርፆ እየሰራ መሆኑን በመጠቆም ከእነዚህም የሞዴል ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶች ግንባታ አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል።

አቶ ማርቆስ አክለውም፤ ትምህርት ቤቱ በአጭር ጊዜ ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ የተባበሩ አካላትን በማመስገን በትምህርት ዘርፎች የተከናወኑ ተግባራት የትምህርት ጥራትና ተደራሽነትን ደረጃ በደረጃ በማሻሻል በኩል ከፍተኛ ሚና እያበረከቱ እንደሚገኙም አስገንዝበዋል።

በመርሃ-ግብሩ የተገኙት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ገበየሁ፤ በዞኑ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን በመገንባትና ምቹ የመማሪያ አካባቢን በመፍጠር ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

አክለውም መንግሥት የትምህርት ጥራት ማረጋገጥ እንዲቻል ከመሠረቱ መጀመር አለበት በሚል ለቅድመ-መደበኛ ትምህርት ልዩ ትኩረት መስጠቱን አቶ ዳዊት ጠቅሰዋል፡፡

በመርሃ-ግብሩ ከክልል፣ የዞኑ ባለድርሻ አካላትና የአካባቢያው ማህበረሰብ ተገኘተዋል፡፡

ዘጋቢ፡ እታገኝ ዘነበ – ከዋካ ጣቢያችን