ከ4 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ እየሰራ መሆኑን የከምባታ ዞን ገቢዎች መምሪያ አስታወቀ

ሀዋሳ፡ ሐምሌ 02/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) በበጀት ዓመቱ በአጠቃላይ ከ4 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ አቅዶ ወደ ሰራ መግባቱን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የከምባታ ዞን ገቢዎች መምሪያ ገለጸ።

በዞኑ በሁሉም መዋቅሮች በ2018/19 የግብር ዘመን ገቢ አሰባሰብ ስራ ማስጀመሪያ መርኃግብር በሺንሸቾ ከተማ ተካሄዷል።

የከምባታ ዞን ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ አሰፋ ከሳሞ እንደገለፁት ከሀምሌ 01/2018 ዓ.ም ጀምሮ በደረጀ”ለ” ግብር ካፋዮች የተጣለባቸውን ግብር ከተያዘው ጊዜ በፊት አንድ ቀን ጊዜ ውስጥ ከፍለው ማጠናቀቅ መቻሉን ገልጸዋል።

ለዚህ ስኬትም የግብር ከፋዩ ያለው ግንዛቤና ቁርጠኝነት የሚበረታታ መሆኑን ጠቁመው፥ ይህም በዞኑ በሁሉም ግብር ከፋዮች ዘንድ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አሳስበዋል።

በተጀመረው በ2019 የበጀት ዓመት 4 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን አቶ አሰፋ አመላክተዋል።

ይህን በወቅቱ በማሳካት ቀጣይ የልማት ስራዎችን ለማፋጠን ያስችል ዘንድ ግብር ከፋዮች በታማኝነት በመክፈል ሀገራዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።

በዞኑ በሺንሽቾ ከተማ አስተዳደር በቀዲዳ ጋሜላ ወረዳ እና ዱራሜ ከተማ አሰተዳዳር አግኝተን ያነጋገርናቸው ግብር ካፋዮች በሰጡን አስተያየት የተጣለባቸውን የገቢ ግብር በወቅቱ እየከፈሉ መሆናቸውን አስረድተዋል።

ዘጋቢ: አለማየሁ ማተቦ – ከሆሳዕና ጣቢያችን