የምርጥ ዘር ችግርን መቅረፍና ማልማት የሚያስችል 1 ሺህ ሄክታር መሬት ከኣሪ ዞን ርክክብ ተካሄደ

የምርጥ ዘር ችግርን መቅረፍና ማልማት የሚያስችል 1 ሺህ ሄክታር መሬት ከኣሪ ዞን ርክክብ ተካሄደ

ሀዋሳ፡ ሰኔ 25/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምርጥ ዘር ድርጅት ከክልሉ አልፎ እንደ ሀገር የምርጥ ዘር ችግርን መቅረፍና ማልማት የሚያስችል 1 ሺህ ሄክታር መሬት ከኣሪ ዞን ርክክብ ማድረጉን አስታወቀ።

የኣሪ ዞን የመንግስት ዋና ተጠሪ እና የብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አፌዶ ወርቁ እንደ ሀገር የግብርና ክፍለ ኢኮኖሚውን በማዘመን እጥፍ ምርታማነትን ለማረጋገጥ እየተሠራ ነው ብለዋል።

በዚህ ሂደት ርክክብ የተፈፀመው መሬት ተጨማሪ አቅም የሚፈጥር በመሆኑ እንደ ዞን የምርጥዘር አቅርቦት ችግር ለመቅረፍ ፋይዳው የጎላ ነው ሲሉም አቶ አፌዶ ገልፀዋል።

የክልሉ መንግስት በኣሪ ዞን ደቡብ ኣሪ ወረዳ ምርጥ ዘር ብዜት ለመምረት እየሰጠ ያለው ትኩረት የሚደነቅ መሆኑን አመላክተዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምርጥ ዘር ድርጅት ዋና ሥራ አስአኪጅ አቶ ብርሃኑ ግዛው ምርትና ምርታማነትን ለማረጋገጥ ምርጥ ዘር በተገቢው በስፋት መሠራት አለበት ብለዋል።

ርክክብ የተፈፀመው መሬት ሳይለማ ታጥሮ የሚቆይ መሆን እንደሌለበት ያሳሰቡት ሀለፊው ሥራውን በቅንጅት መምራት እንደሚያስፈልግ ጠቁመው፥ አካባቢው የዘር ብዜት ክላስተር በሚሆን መልኩ ማልማት እንደሚጠበቅ ጠቅሰው መሬት ለሥራው ምቹ ነው ሲሉም ገልፀዋል።

መሬቱን በአጭር ጊዜ ምቹ በማድረግ ላበረከተው ለአካባቢው መስተዳዳር አመስግነዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትልና የምርጥ ዘር ድርጅት ቦርድ ተወካይ እንዲሁም የዕለቱ የግብርና ቢሮ ኃለፊ ተወከይ አቶ ግዳልቅ አልቅሚ መሬቱ ለምርጥ ዘር ብዜት ከአየር ንብረት ጀምሮ ምቹ በመሆኑ ይህ ትልቅ ስኬት ነው ብለዋል።

ክልሉ ምርጥ ዘር ችግርን በራሱ አቅም ለመሸፈን እየሠራ ሲሆን በዚህም አመርቂ ውጤት መገኘቱን ተናግረው፥ ርክክብ የተፈፀመው መሬት ተጨማሪ አቅም ይፈጥራል ብለዋል።

ሥራው ለወጣቶች ሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ የአካባቢው አርሶ አደሮች ምርጥ ዘርን በቅርበት ማግኘት የሚችሉበት ዕድልን ይፈጥራል።

የኣሪ ዞን ኢንቨስትመንት ጽ/ቤት ሀለፊ አቶ ፍቅረስላሴ ጀማል ለክልሉ ምርጥ ዘር ድርጅት ከዞኑ ዋና አስተዳደር ጋር በመናበብና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመስማት 1 ሺህ ሄክታር እንዲሰጥ መወሰኑን አስረድተዋል ።

ምርጥ ዘር ድርጅቱም የተረከበውን መሬት በአግባቡ ማልማት እንዳለበት አሳስበዋል።

ርክክብ የተፈፀመው መሬት በኣሪ ዞን ደቡብ ኣሪ ወረዳ ጨለጎድ ቀበሌ እንደሆነ ታውቋል።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን