‎የተጎዱ የእርሻ መሬቶችን በተፈጥሯዊ ማዳበሪያ እንዲያገግሙ ለማድረግ እየተካሄደ ያለው የቨርሚ ኮምፖስት ምርምር፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ አንድ ወጥ የአጠቃቀም መመሪያና የፖሊሲ አቅጣጫ ለማዘጋጀት ጠቃሚ ግብዓት እንደሚሆን ተገለጸ

‎የተጎዱ የእርሻ መሬቶችን በተፈጥሯዊ ማዳበሪያ እንዲያገግሙ ለማድረግ እየተካሄደ ያለው የቨርሚ ኮምፖስት ምርምር፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ አንድ ወጥ የአጠቃቀም መመሪያና የፖሊሲ አቅጣጫ ለማዘጋጀት ጠቃሚ ግብዓት እንደሚሆን ተገለጸ

‎የቨርሚ ኮምፖስት የንጥረ ነገር ይዘትና ተገቢ የአጠቃቀም መጠንን ለመወሰን እየተካሄደ ያለው ምርምር፤ የተጎዱ የእርሻ መሬቶች እንዲያገግሙ ለማድረግና የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ ጉልህ አስተዋፅኦ እንደሚኖረው ተጠቁሟል።


‎ከፎሉር ፕሮጀክት ዋና ዓላማዎች መካከል አንዱ የተጎዱ የእርሻ መሬቶችን እንዲያገግሙ ማድረግ መሆኑን በፕላን ሚኒስቴር የፎሉር ፕሮጀክት የአካባቢና የማህበረሰብ ደህንነት ጥበቃ ኦፊሰር ዶ/ር በውቀቱ ኃይሌ ገልጸዋል።

‎ዶ/ር በውቀቱ እንደገለጹት፥ ኮምፖስትና ቨርሚ ኮምፖስት የተፈጥሮ ማዳበሪያዎችን በአግባቡ መጠቀም የአፈር ለምነትን አሻሽሎ የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያበረክታል።

‎አርሶ አደሮች ቨርሚ ኮምፖስትን በባለሙያዎች የግንዛቤ ስልጠናና የግብዓት ድጋፍ በማግኘት ሲያዘጋጁ በውስጡ የሚገኙ ንጥረ ነገሮች መጠን እና በአንድ ሄክታር መሬት የሚያስፈልገው የአጠቃቀም መጠን በትክክል እንዲወሰን ምርምር እየተካሄደበት መሆኑንም አስረድተዋል።

‎በተጨማሪም አርሶ አደሮች በየአካባቢው የተለያዩ የአዘገጃጀት ዘዴዎችና ግብዓቶችን እየተጠቀሙ በመሆናቸው ልምዶቻቸውን በማሰባሰብ ለመላው ሀገሪቱ በወጥነት የሚያገለግል የአጠቃቀም ምክረ ሐሳብ ለማዘጋጀት እየተሠራበት መሆኑን አብራርተዋል።

‎ከሀዋሳ፣ ጅማና አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲዎች እንዲሁም ከኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የተውጣጡ የአፈር ተመራማሪዎች በሀገሪቱ ከተመረጡ 10 ወረዳዎች የቨርሚ ኮምፖስት ናሙናዎችን በመሰብሰብ የላቦራቶሪ ምርመራ እያካሄዱ መሆናቸውንም ጠቁመዋል።

‎የምርምር ውጤቱ ይፋ ከሆነ በኋላ በሀገር አቀፍ ደረጃ የአጠቃቀም ምክረ ሐሳብ እንደሚዘጋጅ እና ለወደፊቱም የፖሊሲ አቅጣጫ ለማስቀመጥ ግብዓት እንደሚሆን ዶ/ር በውቀቱ ገልጸዋል።

‎ተግባሩ የአርሶ አደሮችን ምርታማነት በማሳደግ ዘላቂ የግብርና ልማትን ለማረጋገጥ ጉልህ አስተዋፅኦ እንደሚኖረውም ተገልጿል።

‎ዘጋቢ፡ ውብሸት ካሳሁን – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን