የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በእንሰት ዘር ብዜት ላይ በትኩረት እየተሠራ መሆኑ ተገለፀ

የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በእንሰት ዘር ብዜት ላይ በትኩረት እየተሠራ መሆኑ ተገለፀ

‎የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በእንሰት ዘር ብዜት ላይ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን በጌዴኦ ዞን የራጴ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ።

‎በወረዳው ሁሉም ቀበሌዎች እንሰት አብቃይ መሆናቸውንና የእንሰት ፉንታ(ሀምቾ) ቆረጣ ሥራ መጀመሩን የወረዳው ትምህርት ጽ/ቤት ኃላፊና የዋና አስተዳዳሪ ተወካይ አቶ ኢያሱ ጥላሁን ተናግረዋል፡፡

‎በአንድ ጀምበር የተለዩ ከ61 ሺህ በላይ ፉንታዎች መቆረጣቸውን የጠቆሙት አቶ ኢያሱ፥ በአጠቃላይ ከሚቆረጡ ከ168ሺህ ፉንታዎች ወደ 10 ሚሊዮን የሚጠጋ የእንሰት ችግኝ እንደሚጠበቅ አስረድተዋል፡፡

‎ከእንሰት ችግኝ ብዜት ሥራ ጎን ለጎን የአመራረት ዘይቤን በቴክኖሎጂ በማስደገፍ የአርሶ አደሩን የምግብ ሉዓላዊነት ከማረጋገጥ ባለፈ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ የምርታማ አከባቢዎችን ተሞክሮ የማስፋፋት ሥራ በትኩረት እየተተገበሩ መሆናቸውን የወረዳው ግብርና ጽ/ቤት ምክትል እና የእርሻ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ገዛኸኝ ደያሶ አስታውቀዋል፡፡

‎በአንድ ጀምበር የሀምቾ ቆረጣ መረሐ-ግብር ላይ አግኝተን ካነጋገርናቸው የወረዳው አርሶ አደሮች መካከል ገብሬ ሆርዶፋ፣ ብርሃኑ በራሶና ሌሎችም በቂ የእንሰት ችግኞችን በማዘጋጀት ከራሳቸው አልፎ ለገበያ በማቅረብ የገቢ አማራጫቸውን ለማስፋት ተግተው እየሠሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

‎በዞኑ አንዳንድ አከባቢዎች እንሰት ሁለት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ለምግብነት እየደረሰ መሆኑን በተጨባጭ ማየታቸውን የጠቆሙት አርሶ አደሮቹ ቀደም ሲል በአከባቢው አንድ እንሰት ለምግብነት የሚደርሰው ከአምስት ዓመት በኋላ እንደነበር አስረድተዋል፡፡

‎ይህም ረጅም ዓመት ቆይታ በምርታማነታቸው ላይ አሉታዊ ጫና እያሳደረ መሆኑን የገለጹት አርሶ አደሮቹ የተሻሉ ተሞክሮዎችን በመተግበርና የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን የተዘረጉ ስትራቴጂዎችን በመከተል ምርትና ምርታማነታቸውን ለማሳደግ እንደሚሠሩ አረጋግጠዋል፡፡

‎ዘጋቢ: ሳሙኤል በቀለ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን