የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በእንሰት ዘር ብዜት ላይ በትኩረት እየተሠራ መሆኑ ተገለፀ
የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በእንሰት ዘር ብዜት ላይ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን በጌዴኦ ዞን የራጴ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ።
በወረዳው ሁሉም ቀበሌዎች እንሰት አብቃይ መሆናቸውንና የእንሰት ፉንታ(ሀምቾ) ቆረጣ ሥራ መጀመሩን የወረዳው ትምህርት ጽ/ቤት ኃላፊና የዋና አስተዳዳሪ ተወካይ አቶ ኢያሱ ጥላሁን ተናግረዋል፡፡
በአንድ ጀምበር የተለዩ ከ61 ሺህ በላይ ፉንታዎች መቆረጣቸውን የጠቆሙት አቶ ኢያሱ፥ በአጠቃላይ ከሚቆረጡ ከ168ሺህ ፉንታዎች ወደ 10 ሚሊዮን የሚጠጋ የእንሰት ችግኝ እንደሚጠበቅ አስረድተዋል፡፡
ከእንሰት ችግኝ ብዜት ሥራ ጎን ለጎን የአመራረት ዘይቤን በቴክኖሎጂ በማስደገፍ የአርሶ አደሩን የምግብ ሉዓላዊነት ከማረጋገጥ ባለፈ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ የምርታማ አከባቢዎችን ተሞክሮ የማስፋፋት ሥራ በትኩረት እየተተገበሩ መሆናቸውን የወረዳው ግብርና ጽ/ቤት ምክትል እና የእርሻ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ገዛኸኝ ደያሶ አስታውቀዋል፡፡
በአንድ ጀምበር የሀምቾ ቆረጣ መረሐ-ግብር ላይ አግኝተን ካነጋገርናቸው የወረዳው አርሶ አደሮች መካከል ገብሬ ሆርዶፋ፣ ብርሃኑ በራሶና ሌሎችም በቂ የእንሰት ችግኞችን በማዘጋጀት ከራሳቸው አልፎ ለገበያ በማቅረብ የገቢ አማራጫቸውን ለማስፋት ተግተው እየሠሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
በዞኑ አንዳንድ አከባቢዎች እንሰት ሁለት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ለምግብነት እየደረሰ መሆኑን በተጨባጭ ማየታቸውን የጠቆሙት አርሶ አደሮቹ ቀደም ሲል በአከባቢው አንድ እንሰት ለምግብነት የሚደርሰው ከአምስት ዓመት በኋላ እንደነበር አስረድተዋል፡፡
ይህም ረጅም ዓመት ቆይታ በምርታማነታቸው ላይ አሉታዊ ጫና እያሳደረ መሆኑን የገለጹት አርሶ አደሮቹ የተሻሉ ተሞክሮዎችን በመተግበርና የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን የተዘረጉ ስትራቴጂዎችን በመከተል ምርትና ምርታማነታቸውን ለማሳደግ እንደሚሠሩ አረጋግጠዋል፡፡
ዘጋቢ: ሳሙኤል በቀለ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን
የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በእንሰት ዘር ብዜት ላይ በትኩረት እየተሠራ መሆኑ ተገለፀ

More Stories
በዳውሮ ዞን ታርጫ ከተማ የጥምቀት በዓል በተለያዩ ሀይማኖታዊ ክዋኔዎች በድምቀት ተከብሯል
የ1447ኛው ዓመተ ሂጅራ የሀጅ ምዝገባ ጥር 18 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚጠናቀቅ የሲዳማ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት አስታወቀ
በኮንታ ዞን አመያ ከተማ የጥምቀት በዓል በደማቅ ሁኔታ ተከብሯል