የፌዴሬሽን ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባውን ማካሄድ ጀመረ

የፌዴሬሽን ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባውን ማካሄድ ጀመረ

ሀዋሳ፡ ሰኔ 27/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) የኢፌዴሪ የፌዴሬሽን ምክር ቤት 6ኛ የፓርላማ ዘመን፣ 2ኛ ዓመት የሥራ ጊዜ፣ 2ኛ መደበኛ ስብሰባውን በዛሬው ዕለት በምክር ቤቱ የጉባኤ አዳራሽ ማካሄድ ጀምሯል፡፡

ምክር ቤቱ ስድስተኛ የፓርላማ ዘመን 2ኛ ዓመት የሥራ ጊዜ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በደቡብ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ይኖሩ የነበሩ የስድስት ዞኖችና የአምስት ልዩ ወረዳዎች ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ያካሄዱትን ሕዝበ ውሳኔ አስመልክቶ የሚያቀርበውን ሪፖርት ማዳመጥና ሕዝበ ውሳኔውን አስመልክቶ በቋሚ ኮሚቴው የሚቀርበውን የውሳኔ ሐሳብ መርምሮ ማጽደቅ የሚሉና ሌሎች መደበኛ የመወያያ አጀንዳዎች በማጽደቅ ውይይቱን ቀጥሏል፡፡

ምክር ቤቱ ያጸደቃቸው አጀንዳዎች ላይ በዝርዝር ተወያይቶ ውሳኔ እንደሚያሳልፍባቸው ይጠበቃል።

ጉባኤው ለቀድሞ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አባልና የማንነት፣ የአስተዳደር ወሰንና የሰላም ግንባታ ቋሚ ኮሚቴ አባል ለነበሩትና በቅርቡ ሕይወታቸው ላለፈው የተከበሩ አቶ ግርማ የሺጥላ የሕሊና ፀሎት መደረጉን ከፌዴሬሽን ምክር ቤት የተገኘ መረጃ ያመለክታል፡፡