ባለፉት ጊዜያት በህዝብና በመንግስት መካከል ያለውን ግንኙነት ያጠናከሩ ተግባራት መከናወናቸውን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል መንግስት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ገለጸ
ሀዋሳ፣ ጥቅምት 04/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) ባለፉት ጊዜያት በህዝብና በመንግስት መካከል ያለውን ግንኙነት ያጠናከሩ ተግባራት መከናወናቸውን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል መንግስት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ገልጿል፡፡
“በአጋርነት የዳበረ ኮሚዩኒኬሽን ለህዝብ እምነትና ለሀገር ብልጽግና” በሚል መሪ ሀሳብ ከሁሉም ዞኖችና ከተማ አስተዳደሮች ከተውጣጡ የዘርፉ ባለሙያዎችና የስራ ኃላፊዎች ጋር የውይይት መድረክ በቦንጋ ከተማ እየተደረገ ይገኛል።
በመድረኩን የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የክልሉ መንግስት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ የሺዋስ ዓለሙ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በተጠናቀቀበትና የተፈጥሮ ጋዝ ማምረት በተጀመረበት ማግስት መከናወኑ መድረኩን ልዩ ያደርገዋል ብለዋል።
በእነኚህ ሁሉ እንቅስቃሴዎች ውስጥ የሚዲያና የኮሚዩኒኬሽን ስራዎች የማይተካ ሚና እንደነበራቸው ገልጸዋል።
በዚህ መነሻ ባለፉት ጊዜያት በህዝብና በመንግስት መካከል ያለውን ግንኙነት ያጠናከሩ የህትመት፣ የማህበራዊ ሚዲያ፣ የቴሌቪዥንና የሬድዮ ስራዎች መከናወናቸውን ተናግረዋል።
የብልጽግና ጉዞን እውን የሚያደርጉ የዘርፉ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።
በተለይም በድህረ-እውነት ዘመን የሀሰት የማህበራዊ ሚዲያ ገፆችን እና ህዝብን ከአመራሩ የሚያጋጩ የሀሰት መረጃዎችን ለማስቀረት ፈጣንና በመረጃ የበለጸገ የአሰራር ስርዓት መዘርጋት ያስፈልጋል ብለዋል።
በቀጣይም የህዝቦች የጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመረኮዘ፣ የሀሳብ የበላይነትን ያረጋገጠ የሚድያና ኮሚዩኒኬሽን ስራን ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑን አቶ የሺዋስ አጽንኦት ሰጥተዋል።
በመድረኩ የተገኙት የክልሉ መንግስት ረዳት ተጠሪ አቶ ነጋ አበራ ሀገራችን ኢትዮጵያ የማንሰራራት ጊዜ ላይ በምትገኝበት በዚህ ወቅት የሚዲያና ኮሚዩኒኬሽን ስራዎች ወሳኝ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በተለያዩ አማራጮች መረጃዎች በተበራከቱበት በዚህ ወቅት የዘርፉ ስራዎች ህዝብንና መንግስትን በሚያስተሳስሩ ጉዳዮች ላይ ሊያተኩሩ ይገባል ሲሉ አሳስበዋል።
አብሮነትን የሚሸረሽሩ ከፋፋይ አጀንዳዎችን ማስወገድ ያስፈልጋል ያሉት አቶ ነጋ፤ ስራዎቻችን ከመደመር እሳቤ የተቀዱ መሆን ይኖርባቸዋል ብለዋል።
በቀጣይም ብልጽግናን በሚያረጋግጡ ጉዳዮች ላይ በማተኮር በህዝብና መንግስት መካከል ያለውን ግንኙነት ማጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል።
ዘጋቢ፡ ትዕግስቱ ጴጥሮስ – ከቦንጋ ጣቢያችን

More Stories
የታላቁ ህዳሴ ግድብን እንዳጠናቀቅን ሁሉ የባህር በርን ለማስመለስ የሚደረገውን ጥረት በይበልጥ ማገዝ እና መደገፍ እንደሚገባ ተጠቆመ
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ፋይናንስ ቢሮ ከፌደራል ገንዘብ ሚኒስቴር እና ከክልሉ አመራር አካዳሚ ጋር በመተባበር በመንግስት ፋይናንስ አስተዳደር ዙሪያ ለኦዲት ባለሙያዎች ሲሰጥ የነበረው ስልጠና ተጠናቋል
ህገወጥ የዋጋ ጭማሪ ባደረጉ የንግድ ተቋማት ላይ እርምጃ መወሰዱ ተገለጸ