በያሆዴ በዓል ወቅት የሚደረገው ሲምፖዚየም ለሀገር ልማትና አንድነት ያለው ፋይዳ ከፍተኛ መሆኑ ተገለጸ

በያሆዴ በዓል ወቅት የሚደረገው ሲምፖዚየም ለሀገር ልማትና አንድነት ያለው ፋይዳ ከፍተኛ መሆኑ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ መስከረም 12/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሀዲያ ብሔር ዘመን መለወጫ ያሆዴ በዓል ወቅት የሚደረገው ሲምፖዚየም የብሄሩን ማህበራዊ፣ኢኮኖሚያዊ እና ባህላዊ ዕሴቶችን ለማሳደግ ፣ለሀገር ልማትና አንድነት ያለው ፋይዳ ከፍተኛ መሆኑን የኢፌዴሪ ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶክተር ኤርጎጌ ተስፋዬ ገለጹ።

የሀዲያ ብሄር የባህል፣ ታሪክ፣ ቋንቋና ልማት ስምፖዚየም በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።

በስፖዚየሙ ላይ የተገኙት የኢፌዴሪ ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶክተር ኤርጎጌ ተስፋዬ፥ የስምፖዚየሙ ዋና ዓለማ የሀዲያ ብሄር ከኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች ለሀገር ሰላም፣ አንድነት እና እድገት በጋራ እንዲቆሙ የሚመክርበት የጋራ ዓለማ እና ሀሳብ የሚይዙበት መሆኑን ተናግረዋል።

የሀዲያ ዘመን መለወጫ ያሆዴ በዓል ወቅት የሚደረገው ሲምፖዚየም የብሄሩን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ባህላዊ ዕሴቶችን ለማሳደግና ለሀገር ልማትና አንድነት ያለው ፋይዳ ከፍተኛ መሆኑንም ዶክተር ኤርጎጌ ጠቁመዋል።

የሀዲያ ብሄር በ12ኛ እና 13ኛ ክፍለ ዘመን የራሱ ንጉስ የነበረውና ለአድዋ ድል፣ ለህዳሴ ግንባታ እና በሌሎች ሀገራዊ ልማት፣ ሰላምና አንድነት ከፍተኛ ድርሻ የተወጣ እና እየተወጣ የሚገኝ ሲሆን ይህንን ተሞክሮ ለቀጣይ አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም አሳስበዋል።

በመድረኩ የሀዲያን ባህላዊ አለባበስ፣ አመጋገብ፣ የበዓላት አከባበር፣ የስራ ባህል፣ የመተጋገዝ፣ የጢግ ጉለና ሌሎች ባህላዊ ዕሴቶችን የሚገልጽ ጥናታዊ ጽሁፍ ቀርቦ ሰፊ ውይይት እየተደረገ ነው።

በመርሐ ግብሩ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅ/ፅ/ቤት ኃላፊ ዶ/ር ዲላሞ ኦቶሬ፣ የሀድያ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማቲዎስ አኒዮ እና ሌሎች የፌዴራልና የክልል አመራሮች ተሳትፈዋል፡፡

ዘጋቢ: ሳሙኤል መንታሞ – ከሆሳዕና ጣቢያችን