ከዚህ ቀደም ከባንኩ የብድር አገልግሎት ያገኙ ግለሰቦችም ሆኑ ማህበራት እስከ ሰኔ 23/2015 ዓ.ም ድረስ የወሰዱትን ብድር የሚመልሱ ከሆነ ከቅጣት ነጻ እንደሚሆኑ ተገለጸ
ሀዋሳ፡ ሰኔ 10/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) ከዚህ ቀደም ከባንኩ የብድር አገልግሎት ያገኙ ግለሰቦችም ሆኑ ማህበራት እስከ ሰኔ 23/2015 ዓ.ም ድረስ የወሰዱትን ብድር የሚመልሱ ከሆነ ከቅጣት ነጻ እንደሚሆኑ የኦሞ ባንክ ቦንጋ ዲስትሪክት አስታወቀ።
የአሰራር ስርዓቱን በማሻሻል የአነስተኛ ብድር እና ቁጠባ አገልግሎቶችን ከባንክ ሥራ ጋር በማጣመር እያከናወነ እንደሚገኝ ተገልጿል።
ባንኩ ከዚህ ቀደም የማይክሮ ፋይናንስ አገልግሎት አየሰጠ ባለበት ወቅት ከፍተኛ ብድሮችን መውሰድ የማይችሉና በአነስተኛ የኑሮ ደረጃ ያሉ የህብረተሰብ ክፍሎች አገልግሎቱን በአግባቡ ማግኘት እንዲችሉ ብብዙ መልኩ ሲሰራ መቆየቱን የዲስትሪክቱ ስራ አስኪያጅ አቶ አስራት ኋይሌ ተናግረዋል።
አሁንም ደንበኞች ይህንኑ አገልግሎት እንዲያገኙ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን የገለፁት ስራ አስኪያጁ በካፋ ዞን በ16 ቅርንጫፎች በገጠር እና በከተማ ግብርና፣ በጥቃቅን እና አነስተኛ እንዲሁም በሌሎች የሥራ መስኮች ለተሰማሩ የህብሰተሰብ ክፍሎች የብድር አገልግሎት በመስጠት ደንበኞች ኑሮአቸውን እንዲያሻሽሉ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።
በዚህም በካፋ ዞን እስካሁን ከ 1 መቶ 78 ሺ በላይ ለሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ የብድር አገልግሎት ተደራሽ የተደረገ ሲሆን ከዚህም ማስመለስ የተቻለው 1 ነጥብ 6 ቢሊዮን 7 መቶ 21 ሺ ብር ያህሉን ነው ብለዋል።
የተቀረውን የብድር ገንዘብ ለማስመለስ ከተለያዪ አካላት ጋር እንቅስቃሴዎች እየተደረጉ መሆኑን የገለጹት አቶ አስራት ብድር ወስደው በወቅቱ ያልመለሱ ደንበኞች እስከ ሰኔ 23 ቀን 2015 ዓ.ም ድረስ የሚመልሱ ከሆነ ከቅጣት ነጻ እንደሚሆኑ ተናግረዋል።
ስለሆነም በተቀሩት ቀናት ደንበኞች የወሰዱትን ገንዘብ ተመላሽ በማድረግ የባንኩን የቀጣይ እቅድ ውጤታማ ለማድረግ የበኩላቸውን እንዲወጡ አቶ አስራት ጥሪ አስተላልፈዋል።
ዘጋቢ: ትዕግስቱ ጴጥሮስ – ከቦንጋ ጣቢያችን
More Stories
ከ5 መቶ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሮች እየተሰራጨ መሆኑ ተገለጸ
የትራንስፖርት ዘርፍ አገልግሎቱን ለማዘመን ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ አስታወቀ
የትምህርት አጀንዳ “የሁሉም ልማት በኩር አጀንዳ ነው” ሲሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ ገለፁ