ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣውን የኑሮ ውድነት ለማረጋጋት ያልታረሱ መሬቶችን ማልማት እንደሚገባ ተገለጸ
ሀዋሳ፡ ሰኔ 07/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣውን የኑሮ ውድነት ለማረጋጋትና ተጨማሪ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ያልታረሱ መሬቶችን በስፋት ማልማት እንደሚገባ ተገለጸ።
የዲላ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ ማህበረሰብ አገልግሎት ዘርፍ በዘንድሮው የበልግ ወቅት ከ20 ሄክታር በላይ መሬት በወቅታዊ ሰብሎች መሸፈኑን ገልጿል።
የዲላ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ ዲን አቶ ተረፈ ሾንጦ እንደገለጹት፥ ኮሌጁ የመማር ማስተማር፣ የጥናትና ምርምርን ጨምሮ የማህበረሰብ አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን በተቋሙ ግቢ ውስጥ የሚገኘውን ሰፊ መሬት ለማልማት የተፈለገበት ዋነኛው ምክንያት፥ ምርቱን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ የአከባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚ ለማድረግና በዚሁ አጋጣሚ የውስጥ ገቢን ለማሳደግ መሆኑን ጠቁመዋል።
በዘንድሮው የበልግ ወቅት ከ20 ሄክታር በላይ መሬት በወቅታዊ ሰብሎች መሸፈኑን የገለጹት አቶ ተረፈ በቂ ምርት እንደሚጠብቁና ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣውን የኑሮ ውድነት ለማረጋጋት ተጨማሪ ምርት ማምረት እንደሚያስፈልግ ተናረዋል።
በኮሌጁ የስነ-ትምህርት ሳይንስ መምህርና የማህበረሰብ አግልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ተዘራ ጌታሁን በበኩላቸው፥ አምና በተሠራው የግብርና ሥራ ማበረታቻ የውሃ መሳቢያ ፓምፕ ሽልማት ማግኘታቸው የበለጠ እንዲሰሩና በዘንድሮው የበልግ ወቅት በስፋት የተለያዩ ሰብሎችን እያለሙ እንደሚገኙ ጠቁመዋል፡፡ ምርቱ ሲደርስ ነጋዴው ከነጋዴ ሰንሰለት በመፍጠር እያስከተለ ያለውን የዋጋ ንረት ለማስቀረት ቀጥታ ለተጠቃሚዎች የሚያቀርቡበት አሰራር ለመዘርጋት ዕቅድ እንዳላቸው አስረድተዋል።
ከእርሻ ኮሚቴ አባላት መምህርት የሺሐረግ ግርማና መምህር ዘገዬ ማንደፍሮ በተቋሙ ስም የተካለለው መሬት በጣም ሰፊ ሲሆን ያለምንም አገልግሎት ቆይቶ እንደነበር አስተውሰው፥ ዘንድሮ በቆሎ በስፋት እንደተዘራበትና የዝናብ ሁኔታውም ተስፋ ሰጪ በመሆኑ ጥሩ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል::
ከአከባቢው ማህበረሰብም ተጠቃሚ ከሆኑ አርሶ አዶሮች መካከል አቶ አብርሃም አያሌው በአሁኑ ወቅት ሰብሉ ያለበት ሁኔታ በእይታ የሚያጠግብ ነው በማለት ሁሉም ማህበረሰብ ባለው መሬት እንደዚሁ ቢያለማ መልካም ነው ሲሉ አስተያየታቸውን አጋርተውናል።
ዘጋቢ፡ ምርጫ መላኩ – ከፍስሃገነት ጣቢያችን

More Stories
ከመማር ማስተማር ተግባር ባለፈ የአካባቢ ማህበረሰብ ተጠቃሚነት ላይ ትኩረት አድርጎ እየሰራ መሆኑን የሚዛን ግብርና ቴክኒክ ሙያ ትምህርትና ስልጠና ኮሌጅ አስታወቀ
የኢፌዲሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ(ዶ/ር) መጭው ጊዜ ከተስፋ ብርሃን ወደሚጨበጥ ብርሃን የምንሸጋገርበት ብሩህ ዘመን መሆኑን ተናገሩ
በተቀሩት አጭር ቀናት ህብረተሠቡ የመራጭነት ካርዱን በመውሰድ የዜግነት ግዴታውን እንዲወጣ የጎፋ ዞን መሎ ኮዛ ወረዳና አካባቢው የፌደራልና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ጥሪ አቀረቡ