የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት የፋይናንስ ጉባኤ እየተካሄደ ነው
ሀዋሳ፡ ሰኔ 08/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት 6ኛ አጠቃላይ የፋይናንስ ጉባኤ በስካይ ላይት ሆቴል እየተካሄደ ነው፡፡
በጉባኤው ላይ ከ300 በላይ በፋይናንስ ሴክተር ሙያ ውስጥ ያሉ የዘርፉ መሪዎች፣ ፖሊሲ አውጪዎችና አማካሪዎች፣ የመንግስትና የግል ተቋማት፣ የአለም አቀፍ ኩባንያዎች ተወካዮች፣ የኢኮኖሚ ተንታኞችና ተመራማሪዎችን ጨምሮ ሌሎችም በዘርፉ አንቱ የተባሉ በምስራቅ አፍሪካና በሌሎችም ሀገራት የሚገኙ የፋይናንስ ተቋማት ተሳትፈዋል።
ለፖሊሲ አውጪዎችና አጥኚዎች መላ የሚያቀብሉ የጥናት ወረቀቶችም ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል ተብሎ ይጠበቃል።
የአይ_ካፒታል አፍሪካ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ገመቹ ዋቅቶላ እንደገለጹት ለሁለት ቀናት በሚዘልቀው በዚሁ ጉባኤ የፋይናንስ አካታችነት፣ የአፍሪካ ቀጠና ኢኮኖሚ ጉዞና የኢትዮጵያ አሁናዊ የፋይናንስ አስተዳደር ሥርዓት፣ የካፒታል ገበያ፣ የዲጅታል ፋይናንስ ጉዞ እንዲሁም የፋይናንስ ሊበራላይዜሽን ዙሪያ ያለው አጠቃላይ የፖሊሲ ውሳኔና ተግባራቸው ይፈተሻል።
ከዚህ በፊት የተካሄዱ አምስቱ የምስራቅ አፍሪካ አገራት ፋይናንስ ጉባኤዎች አዳዲስ ሀሳቦችን ወደፊት አምጥቷል ብለዋል።
ይኸኛው ጉባኤ ከምስራቅ አፍሪካ የፋይናንስ አቅጣጫዎች በተጨማሪ በዓለም አቀፍና ቀጠናዊ የፋይናንስ ችግሮች ዙሪያ በመምከር የቀጣይ መፍትሄ አማራጮችን ያስቀምጣል ተብሎም ይጠበቃል።
ጉባኤውን ያዘጋጁት አይ_ካፒታል አፍሪካ ኢንስትቲዩት፣ የኢትዮጵያ መድን ሰጪዎች ማህበር ከኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን እና ከሌሎችም ጋር በመተባበር ነው።
ዘጋቢ፡ ጌታሁን አንጭሶ

More Stories
የግል እና የጋራ መጸዳጃ ቤቶችን በተገቢው በመጠቀም ተላላፊ የሆኑ በሽታዎችን አስቀድሞ መከላከል እንደሚገባ በጉራጌ ዞን የእኖር ወረዳ ጤና ጥበቃ ጽህፈት ቤት አስገነዘበ
12 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በተቋማት የድርጊት መርሐ-ግብርና በፀደቀላቸው በጀት መሠረት ማሰራጨቱን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ፋይናንስ ቢሮ አስታወቀ
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) በምስራቅ ጉራጌ ዞን ቡኢ ከተማ አስተዳደር እየተገነባ የሚገኘውን ብሉ ኤለፋንት ፋይበር ቦርድ ካምፓኒ ጎበኙ