የክረምት ዝናብን ተከትሎ ጎርፍ እና መሰል አደጋዎች በሰው ህይወትና ንብረት ላይ ጉዳት እንዳያስከትሉ ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ የጋሞ ዞን ግብርና መምሪያ አስታወቀ
ከጎርፍና መሰል አደጋዎች ባሻገር የከሰል እሳት አጠቃቀምም ላይ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልግ መምሪያው ጠቁሟል።
የዘንድሮው የክረምት ዝናብ ጠንከር ያለና ቀጣይነት ያለው መሆኑን የአየር ትንበያ መረጃዎች ይጠቁማሉ።
የጋሞ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊና የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ዘርፍ ኃላፊ አቶ ደርሶ በላይ፤ ሰሞኑን እየጣለ ባለው ዝናብ ምክንያት የመሬት መሸርሸር፣ ናዳ እና ጎርፍ ሊከሰት ስለሚችል የዘርፉ ባለሙያዎች ልየታ በማድረግ ለአደጋ ተጋላጭ አካባቢዎች ላይ የሚገኙ አካላት እንዲነሱ በማድረግ የቅድመ ጥንቃቄ ስራ ሊሰራ ይገባል ብለዋል።
የውሃ ማፋሰሻ ቦዮችን በማፅዳትና ለጎርፍ መውረጃ ማዘጋጀት ይገባል ያሉት አቶ ደርሶ፤ ቆላማ አካባቢዎች ላይ ዝናብ ባይጥል እንኳ ወንዞች በደራሽ ዉሃ መሞላት ሊያጋጥም ስለሚችል ህፃናት ወደ ወንዝ እንዳይሄዱ መጠበቅ እንደሚገባም አስታውቀዋል።
አያይዘውም በክረምት ወራት ብርድን ለመከላከል ተብሎ ጥንቃቄ የጎደለው የከሰል እሳት መጠቀም ለሞት ስለሚዳርግ ከቤት ውጪ ከሰል ማቀጣጠል፣ በቤት ውስጥም በቂ አየር እንዲገባ በማድረግ ሊፈጠር ከሚችል አደጋ ራስን መጠበቅ አስፈላጊ መሆኑን አፅንኦት ሰጥተዋል።
ዘጋቢ፡ ገነት መኮንን – ከአርባምንጭ ጣቢያችን

More Stories
በጎ ተግባር ወቅትን ጠብቆ የሚተገበር ብቻ ሳይሆን የሁልጊዜ ተግባራችንና ባህላችን ልናደርገው ይገባል -ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
“ማሽቃሮ” በዩኔስኮ ለማስመዝገብ በተደረገ ጥናት ላይ ውይይት እየተካሄደ ነው
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የ2018 የክረምት ወራት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ክልል አቀፍ ማስጀመሪያ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል