ለሕዝቡ የሠላም፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ምላሽ መስጠት እንደሚገባ ተገለፀ

ለሕዝቡ የሠላም፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ምላሽ መስጠት እንደሚገባ ተገለፀ

የኧሌ ዞን ሽግግር ምክር ቤት ባካሄደው 6ኛ ዙር 7ኛ መደበኛ ጉባኤው በተለያዩ አጀንዳዎች ላይ ከመከረ በኋላ ለ2018 በጀት አመት ከ426 ሚሊዬን ብር በላይ በጀት በማፅደቅ ተጠናቅቋል።

ምክርቤቱ የ2017 የአስፈፃሚ መሥሪያ ቤቶች፣ የአስተዳደር ምክር ቤት እና የከፍተኛ ፍርድ ቤት የሥራ አፈፃፀም ሪፖርት ገምግሟል፡፡

የዞኑ የሠላም፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች እንዲሁም የመንገድ ፣ የመብራት፣ የንፅሁ መጠጥ ውሃ አቅርቦትና ሌሎች ችግሮች እንዲፈታላቸው የምክር ቤት አባላት ጠይቀዋል።

ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ የግብዓትና የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ፤ የትምህርት ውጤት ስብራትና የማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን አገልግሎት ልዩ ትኩረትን ይሻል ብለዋል።

ከምክር ቤት አባላት ለተነሡ ጥያቄዎች በሴክተር መሥሪያ ቤት ኃላፊዎችና በዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አርሻሌ አርካሎ ምላሽና ማብራሪያም ተሰጥቶባቸዋል ።

በጀትን ለታለመለት ዓላማና ለሕዝብ ተጠቃሚነት ማዋል እንደሚገባ የገለፁት የኧሌ ዞን ሽግግር ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤ ወይዘሮ ውድነሽ ሽቱ በአፈፃፀም ሂደት የነበሩ ጥንካሬዎችና ጉድለቶችን በመለየት የተገልጋይ እርካታን ለማረጋገጥ ይሠራል ብለዋል።

ምክር ቤቱ የ2018 በጀት አመት ዕቅድና ለዞኑ የመንግሥት ሥራዎች አገልግሎት የሚውል 426 ሚሊዮን 81ሺህ 6 መቶ 69 ብር እንዲሆን በሙሉ ድምፅ አጽድቋል ።

ዘጋቢ፡- ተመስገን አሰፋ ከጂንካ ጣቢያችን