የኣሪ ዞን ሽግግር ምክር ቤት 4ኛ ዙር 13ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 5ኛ መደበኛ ጉባኤውን ማካሄድ ጀመረ

የኣሪ ዞን ሽግግር ምክር ቤት 4ኛ ዙር 13ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 5ኛ መደበኛ ጉባኤውን ማካሄድ ጀመረ

ሀዋሳ፡ ሐምሌ 21/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የኣሪ ዞን ሽግግር ምክር ቤቱ 4ኛ ዙር 13ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 5ኛ መደበኛ ጉባኤ የዞኑን አስተዳደር የ2017 ዓ/ም የአስፈጻሚ አካላት ሪፖርት በዝርዝር ማድመጥ ጀምሯል፡፡

ምክር ቤቱ የ2018 ዓ/ም ረቂቅ ዕቅድ፣ በጀት ማጽደቅ እንዲሁም የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የ2017 ዓ/ም አፈፃፀምና የ2018 ዓ/ም ዕቅድና በሌሎች 6 አጀንዳዎች ላይ ይመክራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ምክር ቤቱ በዞኑ ደቡብ ኣሪ ወረዳ በኮመር ቀበሌ በመሬት መንሸራተት አደጋ ህይወታቸውን ላጡ የአንድ ቤተሰብ አባላት የህሊና ፀሎት በማድረግ ጉባኤውን ማካሄድ ጀምሯል ።

የኣሪ ዞን ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ ወ/ሮ ስመኝ ተስፋዬ በጉባኤው ላይ ባስተላለፉት መልዕክት በዞኑ በደቡብ ኣሪ ወረዳ በኮመር ቀበሌ ሐምሌ 13 ቀን 2017 ዓ.ም በመሬት መንሸራተት አደጋ ህይወታቸውን ላጡ የአንድ ቤተሰብ አባላት የተሰማቸውን ሀዘን ገለፀው፥ በአደጋው የተፈናቀሉ ወገኖችን ለማቋቋም ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል ።

ዋና አፈ-ጉባኤ ወ/ሮ ስመኝ ተስፋዬ በዞኑ ማህበራዊ ዘርፍ ባሉ ተቋማት በርካታ ውጤቶች የተመዘገቡ መሆኑን ጠቁመው፥ በትምህርት ዘርፍ በቀጣይ ህጻናት በአፍ መፍቻ ቋንቋ እንዲማሩ በዞኑ ሁሉም ትምህርት ቤቶች የኣራፍ ቋንቋ እንዲሰጥ የዘርፉን መምህራንና ግብአት የማቅረብ ተግባራት በጤና፣ በሴቶች፣ ወጣቶች፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ላይ በትኩረት እንደሚሰራ በመልዕክታቸው አብራርተዋል።

ምክር ቤቱ በተሰጠው ስልጣንና ተግባራት በዞኑ የልማትና መልካም አስተዳደርን የሚያሰፍን የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ውሳኔዎች ማሳለፍ፣ ለማህበራዊ አገልግሎት መስፋፋት ኢኮኖሚያዊ ልማትን ለማፋጠን አስፈላጊ የሆኑ ተቋማትን ማደራጀት ብሎም ሹመቶችን መስጠት የዞኑ የመንግሥት አካላት ዕቅድና በጀት መርምሮ ማጽደቅ ነው ብለዋል።

ዘጋቢ: ጄታ ታገሠ – ከጂንካ ጣቢያችን