የጎፋ ዞን ምክር ቤት 4ኛ ዙር 11ኛ መደበኛ ጉባኤውን በሳውላ ከተማ ማካሄድ ጀመረ‎

የጎፋ ዞን ምክር ቤት 4ኛ ዙር 11ኛ መደበኛ ጉባኤውን በሳውላ ከተማ ማካሄድ ጀመረ‎

‎የጎፋ ዞን ህዝብ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ሀብታምነሽ ግራዝማች ጉባኤውን ሲከፍቱ እንዳሉት፤ ምክር ቤቶች የህዝብ ሉዓላዊነት መገለጫ፣ የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታና በመንግሥት አሰራር የህዝብ ተሳትፎን በማረጋገጥ መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን የሚያደርጉ ዋነኛ ተቋማት ናቸው።

የዞኑ ምክር ቤት በየደረጃው የሚገኙ ምክር ቤቶችን ድጋፋዊ ክትትል በማድረግ በህገ መንግስቱ የተሰጣቸውን ተግባራትና ኃላፊነታቸውን በአግባቡ በመወጣት የመልካም አስተዳደርና የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ሚናቸውን እንዲወጡ ከፍተኛ ዕገዛ እያደረገ መቆየቱን ገልጸዋል።

ህዝባችንን ከተረጂነት በማላቀቅ ምርታማ ለማድረግና የወጣቶችን የስራ ዕድል ለመፍጠር እየተከናወነ ባለው ርብርብ የምክር ቤት አባላት ሚናቸው የላቀ መሆኑን አንስተዋል።

በጉባኤው የዞኑ ህዝብ ምክር ቤት፣ የዞኑ አስተዳደር ምክር ቤትና የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የ2017 በጀት ዓመት ሪፖርትና የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ እንዲሁም የዞኑን የ2018 በጀት ረቂቅና የተለያዩ ሹመቶች ቀርበው ውይይት ከተደረገ በኋላ እንደሚጸድቁ ይጠበቃል።

በጉባኤው የክልልና የዞን ምክር ቤት አባላት እና ጥሪ የተደረገላቸው የመንግስት የስራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ይገኛሉ።

ዘጋቢ፡ አይናለም ሰለሞን – ከሳውላ ጣቢያችን