ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያውያን ልዩ አርማ ሆኖ በታሪክ አሻራ ይመዘገባል ሲሉ የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ ገለፁ
የህዳሴ ዋንጫ ተረኛ ተረካቢ የሆነው ደቡብ ኦሞ ዞን ከኣሪ ዞን በተረከበበት መርሐ ግብር ላይ ተገኝተው ነው የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ ይህንን መልዕክት ያስተላለፉት።
ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን በህብረት ችለናል እንኳን ደስ አላችሁ መልዕክትም ዋና አስተዳዳሪው ለታዳሚው አስተላልፈዋል።
ግድቡ ሲጠናቀቅ ከህዝብ የኤሌክትሪክ ሀይል ፍላጎት ከማሟላት በተጨማሪ በኢንዱስትሪ፣ ኢንቨስትመንት ዘርፍና በሁሉ አቀፍ የኢኮኖሚ ልማት አቅም በመፍጠር እና የመላው ኢትዮጵያዊውን አንድነትን በጽኑ መሠረት ላይ እንዲቆም ትልቅ አቅም ይፈጥራል ብለዋል ዋና አስተዳዳሪው።
እንደ ዞን 22 ሚሊዮን 750 ሺህ ብር በላይ በግድቡ አስተዋጽኦ ማበርከት መቻሉን አቶ ማዕከል ገልፀዋል።
በድጋፍ ማዕቀፍ አስተዋጽኦ ያደረጉ አካላትን ዋና አስተዳዳሪው አመስግነዋል።
በቅርቡ ግድቡን አስመርቀን ኢትዮጵያዊያን በህብረት እንደሚችሉ በዓለም ህዝብ እናስመሰክራለን ሲሉም አቶ ማዕከል ገልፀዋል።
የህዳሴ ዋንጫውን ለሳምንት ያህል ቆይታ ካደረገው ከኣሪ ዞን ተረኛ ለሆነው ለደቡብ ኦሞ ዞን ለማስረከብ በመርሐ ግብሩ የተገኙት የኣሪ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና ከተማና መሠረተ ልማት መመሪያ ሀላፊ አቶ ገረመው ኃ/ማርያም እንደገለፁት፤ ግድቡ በኢኮኖሚ ራሳችንን እንድንችል የብልጽግና ማሳያ ነው።
የዲመካ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ወሌ አልማ፤ ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በመገንባት በዓለም አደባባይ የትኛውንም ግዙፍ ልማት በራስ አቅም ማከናወን እንደምንችል በተግባር አሳይተናልና በዚህም ልዩ ኩራት ይሰማናል ብለዋል።
በቀጣይም ከዚህ የሚበልጥ ትላልቅ ልማቶችን እውን እንደምናደርግ አንድነታችን በራሱ ይመሰክራል ሲሉም ከንቲባው መልዕክት አስተላልፈዋል።
ከተማ አስተዳደሩ አርብቶ አደሩንና የከተማውን ነዋሪ፣ መንግስት ሠራተኞችን እና የተለያዩ አካላትን በማነቃነቅ ለግድቡ ወደ አንድ ሚሊዮን የሚጠጋ ገንዘብ ድጋፍ መደረጉን ገልፀው ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን

More Stories
አርባምንጭ ዩኒቨርስቲ ሳውላ ካምፓስ ለ9ኛ ጊዜ በተለያዩ የሙያ መስኮች ያሰለጠናቸውን 121 ተማሪዎችን አስመረቀ
ዲግሪው “ወረቀት ብቻ ሳይሆን፣ የሀገር ተስፋና የትውልድ ኃላፊነት ነው” – አፈወርቅ ካሱ (ፕ/ር)
በክልሉ የተጀመሩ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የድጋፍና ክትትል ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የመጠጥ ውሃና ሳኒቴሽን ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ዶ/ር አስፋው ዲንጋሞ ገለጹ