የህዝብ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በተሰራው ስራ በሁሉም ዘርፍ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በስልጤ ዞን የምዕራብ አዘርነት በርበሬ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ

የህዝብ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በተሰራው ስራ በሁሉም ዘርፍ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በስልጤ ዞን የምዕራብ አዘርነት በርበሬ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ

የወረዳው የ2017 በጀት አመት ዕቅድ አፈፃፀም እና የቀጣይ ዓመት ዕቅድ ተገምግሟል::

የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ አቶ ረህመቶ ሹክረቶ እንደገለጹት፤ በ2017 በጀት ዓመት የወረዳውን ህዝብ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመፍታት በተሰራው ስራ በሁሉም ዘርፍ ውጤት ማስመዝገብ ተችሏል።

በወረዳው የመልካም አስተዳደር ችግር ሆኖ የቆየውን 17 ሚሊየን ብር ውዝፍ የመንግስት እዳ መክፈል መቻሉን የተናገሩት ዋና አስተዳዳሪው፤ የጤና ባለሙያዎችን የትርፍ ጊዜ ክፍያ መክፈል እንደተቻለ ጠቁመዋል።

የመንገድ እና ንጹህ የመጠጥ የውሃ ተደራሽነት ችግርን ለመፍታት ህብረተሰቡን በማሳተፍ የተሻላ ውጤት የተመዘገበበት አመት እንደነበር ጠቅሰዋል::

በጤናው ዘርፍ በሽታ አስቀድሞ ከመከላከል በተጨማሪ የአገልግሎት አሰጣጥ ተደራሽነትን ለማሻሻል በተሰራው ስራ የአይሳኮ ጤና ኬላ ለአገልግሎት ክፍት ከማድረግ ጀምሮ በሌራ ጤና ጣቢያ የቀዶ ህክምና አገልግሎት ማስጀመር መቻሉን አቶ ራህመቶ አመልክተዋል።

በግብርና ዘርፍ፣ በአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ፣ በአረንጓዴ አሻራ፣ በመኸር፣ በበልግ እርሻ፣ በመስኖ፣ በፍራፍሬና አትክል ልማት ዘርፍ አርሶአደሩን ተጠቃሚ ማድረግ የሚያስችል ስራ መሰረቱን ገልጸዋል::

በትምህርት ጥራት፣ በግብርና ስራ ላይ የክትትል ጉድለት የንጹህ መጠጥ የውሃ ተደራሽነት ችግሮችን ለመፍታት አቅጣጫ መያዙን ዋና አስተዳዳሪ ገልጸዋል።

በቀጣይ የህዝብ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በሚሰራው ስራ ፈፃሚ አካላት የድርሻቸውን እንዲወጡና ህብረተሰቡም ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ዋና አስተዳዳሪው መልዕክት አስተላልፈዋል።

ዘጋቢ: አሚና ጀማል – ከሆሳዕና ጣቢያችን