በጎፋ ዞን በያዝነው የክረምት ወራት ልዩ ልዩ ጠቀሜታ ያላቸው 16 ሚሊዮን ችግኞች ተከላ እንደሚከናወን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ

በጎፋ ዞን በያዝነው የክረምት ወራት ልዩ ልዩ ጠቀሜታ ያላቸው 16 ሚሊዮን ችግኞች ተከላ እንደሚከናወን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ

“በመትከል ማንሰራራት” በሚል መሪ ቃል በጎፋ ዞን ዛላ ወረዳ የአረንጓዴ አሻራ ዞናዊ የችግኝ ተከላ መርሀ ግብር ተካሂዷል።

የችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩን ያስጀመሩት የጎፋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ምናሴ ኤልያስ፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተጨባጭ ዉጤት የተመዘገበበት ሲሆን በዚህም ከሀገር አልፎ የዉጪ ሀገራት ጭምር ጠቀሜታዉን ተረድተዉ እየሰሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል።

በዞኑ ባለፉ ዓመታት ከደረሰው የተፈጥሮ አደጋ ትምህርት ወስደናል ያሉት አቶ ምናሴ፤ ይህንን ለማስቆም ዛሬ የምንተክለው ችግኝ ወሳኝ ነው በማለት እንደዞን በሁሉም መዋቅር አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል።

የጎፋ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ዳንኤል ደግፌ እንደ ዞን 51 ሚሊዮን ችግኞችን በበጀት ዓመቱ ለመትከል ታቅዶ 25 ሚሊዮን ችግኞች በበልግ ወቅት መተከላቸውን ተናግረዋል።

አክለዉም በዚህ ክረምት ወራት 16 ሚሊዮን ችግኝ ይተከላል ያሉ ሲሆን በአንድ ጀምበር 7.5 ሚሊዮን ችግኝ እንደሚተከል ተናግረዋል።

ዘጋቢ፡ አወል ከድር – ከሳውላ ጣቢያችን