የሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት የኑሮ ጫናን ለመቀነስ አጋዥ መሆናቸውን የወልቂጤ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ገለፀ

የወልቂጤ ፖሊቴክኒክ እና ሳተላይት ካምፓስ ሰራተኞች “ይስሬሸ ሀላፊነቱ የተወሰነ የሸማቾች ህብረት ስራ ማህበር” መስርተዋል።

በምስረታ መርሀ ግብሩ ላይ የተገኙት የጉራጌ ዞን ህብረት ስራ ጽህፈት ቤት የህብረት ስራ ማህበራት ማደራጃና ማስፋፊያ ቡድን መሪ አቶ ሀይለኛው ጌታቸው፤ ለማህበረሰቡ በቂ አገልግሎት መስጠት የሚችሉ ሸማች ህብረት ስራ ማህበር በማቋቋም ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።

አቶ ሀይለኛው አክለውም፤ በወልቂጤ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ የተመሠረተው ሸማች ህብረት ስራ ማህበር የግቢው ማህበረሰብን የኑሮ ጫናን ለመቀነስ የሚያስችል መሆኑን በማንሳት የዞኑ ህበረት ስራ ተቋም አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል ያደርጋል ብለዋል።

የወልቂጤ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅና ሳተላይት ካምፓስ ምክትል ዲን እንዲሁም የይስሬሸ ህብረት ስራ ማህበር የበላይ ጠባቂ አቶ አጅመል መሀመድ፤ በተቋሙ ብዙ ሰራተኛ መኖራቸውን በማንሳት የማህበሩ መመስረት በሰራተኞቹ ላይ ያለውን የኑሮ ጫና እንደሚቀንስም ነው ያነሱት።

አቶ አጅመል አክለውም ተቋሙ ለማህበሩ ተገቢውን ድጋፍና ክትትል እንደሚያደርግ ገልፀዋል።

አቶ ጎሳዬ በቀለ የማህበሩ ሰብሳቢ ሲሆኑ የማህበሩ መመስረት ዋና አላማ ለግቢው ማህበረሰብ የተለያዩ ግብአቶችን በአነስተኛ ዋጋ ከማቅረብ አልፎ የውጪውን ማህበረሰብ ማገዝ መሆኑን ጠቁመዋል።

ወ/ሮ ሊዲያ ሳኒ እና መ/ር እንዳሻው ደጀን አስታየታቸው ከሰጡን የማህበሩ አባላት መካከል ሲሆኑ የማህበሩ መመስረት የኑሮ ጫና ለመቀነስ እንደሚጠቅም በማንሳት ከግቢ ውጪ ያለውንም ማህበረሰብ ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ጠቅሰዋል።

ዘጋቢ፡ አስፍር ሙህዲን – ከወልቂጤ ጣቢያችን