ሀዋሳ፡ ሐምሌ 04/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) ለተገልጋዩ ህብረተሰብ ከጠልቃ ገብነት፣ ከዕንግልትና ገንዘብ ብክነት በፀዳ መልኩ በቴክኖሎጂ የተደገፈ አገልግሎት ለመስጠት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን በኢትዮጵያ ኢምግሬሽንና የዜግነት አገልግሎት የሆሳዕና ቅርንጫፍ አስታወቀ።
ቅርንጫፉ ከ2016 ታህሳስ ጀምሮ እስከሁን ከ130ሺ የሚበልጥ ፓስፖርት ለተገልጋይ መስጠቱን አስታውቋል።
የአንድ ሀገር ዜግነትን በአለም አቀፍ የሚገልጸው ፓስፖርት ሲሆን ፓስፖርት የሚሰጠው ተቋም ደግሞ የኢምግሬሽን እና ዜግነት አገልግሎት ነው።
በኢትዮጵያ ፓስፖርት እና ዜግነት አገልግሎት የሆሳዕና ቅርንጫፍ ኃላፊ አቶ አማኑኤል አለሙ እንደገለጹት ቅርንጫፉ በዋናነት ለደቡብ ኢትዮጵያ፣ ለማዕከላዊ ኢትዮጵያ እና በስራና በሌላ ምክንያትም ከተለያዩ አከባቢዎች መጥተው ነዋሪ ለሆኑ ዜጎችም አገልግሎት ይሰጣል።
ፓስፖርት ሳይዙ ወደ ሌላ ሀገር ለመሄድ መሞከር ወንጀልና ህገወጥ መሆኑን የገለጹት አቶ አማኑኤል ማንኛውም ዜጋ አስፈላጊ መስፈርቶችን አሟልቶ ከመጣ ፓስፖርት ማግኘት እንደሚችል ተናግረዋል።
ቅርንጫፉ አዲስ፣ ዕድሳት፣ አስቸኳይ እና የጠፋውን ፓስፖርት የመስጠትና የስም ማስተካከያ አገልግሎቶችን የሚሰጥ ሲሆን እያንዳንዱ አገልግሎት ከህትመት ቁጥርና ከሚሰጠው ኮታ አንጻር የቀጠሮ ቀን ልዩነት እንደሚኖር አቶ አማኑኤል ተናግረዋል።
አብዛኞቹ ተገልጋዮች ከግንዛቤ እጥረት አስፈላጊ መስፈርቶችን ሳያሟሉ እና ሌሎች ተገልጋይ ያልሆኑ ሰዎችን ከጎናቸው ይዘው በሚመጡበት ወቅት በተቋሙ አሰራር ሂደት ላይ ማስተጓጎል ከመፍጠራቸውም ባሻገር ለገንዘብ ብክነት እና ለእንግልት ሊዳርጉ እንደሚችሉ አቶ አማኑኤል ጠቁመዋል።
ከ2016 ታህሳስ ወር ጀምሮ እስከ አሁን ከ130ሺ በላይ ፓስፖርት ለተገልጋይ መስጠት ተችሏል ያሉት አቶ አማኑኤል ከዚህ ውስጥ ከ70 ሺ በላይ በዘንድሮ የተሰጠ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
አገልግሎቶቹ በቴክኖሎጂ የተደገፉ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ፓስፖርት ቁጥርን በማሳደግ የተለያዩ አገልግሎቶችን የያዘ ኤሌክትሮኒክስ አዲስ ፓስፖርት ከመስከረም ወር ጀምሮ ለመስጠት አስፈላጊ ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም ከአቶ አማኑኤል ገለጻ ለማወቅ ተችሏል።
ማንኛውም ተገልጋይ ያልሆነውን ሰው ሳያስከትል በመምጣት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ችግር ካጋጠመ ቢሮ ገብቶ ባለድርሻ በማናገር ችግሮቹን መፍታት ይቻላል ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
በዕለቱ አገልግሎት እያገኙ ከነበሩት አንዳንድ ያነጋገርናቸው ተገልጋዮች በሰጡት አስተያየት ከዚህ ቀደም አገልግሎት ለማግኘት ብዙ መመላለስ፣ ዕንግልትና የገንዘብ ወጪ እንደነበር ገልጸው አሁን ግን በዕለቱ ማግኘት የሚችሉትን አገልግሎት በዕለቱ ጨርሰዉ እየሄዱ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ዘጋቢ: ሳሙኤል መንታሞ – ከሆሳዕና ጣቢያችን

More Stories
በክልሉ የሚገኙ ነዋሪዎችን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል ሥራ በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ገለጹ
የእናቶችንና ጨቅላ ህፃናትን ሞት ለመቀነስ በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርእሰ መስተዳደር (ዶ/ር ) እንዳሻው ጣሰው በተገኙበት በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ምርቃትና የመሰረተ ድንጋይ የማስቀመጥ ስነ-ስረዓት እየተካሄደ ይገኛል