‎ደም መለገስ ለተጎዱ ወገኖች ህይወትን መስጠት፣ የአይን ብሌን መለገስ ደግሞ የህይወት ብርሀን መመለስ መሆኑ ተገለፀ

‎የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት ጤና ቢሮ የበጎ ፍቃድ ደም ለጋሾች እና ተቋማት የምስጋና እና የዕውቅና መርሀ ግብር በወላይታ ሶዶ እየተከናወነ ይገኛል።

‎የደም ለጋሾች ቀን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ21ኛ ጊዜ “የህይወትና የብርሀን ስጦታ ያበርክቱ፤ ደምና ብሌን ይለግሱ” በሚል መሪ ቃል በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወላይታ ሶዶ በመከበር ላይ ይገኛል።

‎‎

‎በዓሉ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በወላይታ ዞን ሶዶ ከተማ የክልልና የዞን ከፍተኛ አመራሮች፣ ከፍተኛ ደም ለጋሾች፣ የደም ልገሳ ማህበራትና ተቋማት በተገኙበት እየተከበረ ይገኛል።

‎በመርሀ ግብሩ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የወላይታ ሶዶ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ አቶ ተፈሪ አባተ፤ በክልሉ 8 ነጥብ 4 ሚሊየን ህዝብ እንደሚኖር አውስተው ደም መለገስ ለተጎዱ ወገኖች ህይወትን መስጠት፣ የአይን ብሌን መለገስ ደግሞ የህይወት ብርሀን መስጠት እንደሆነ ጠቁመዋል።

‎ደም ለጋሾች ጀግኖቻችንና አምባሳደሮቻችን ናቸው ያሉት አቶ ተፈሪ፤ የደምና የአይን ብሌን ልገሳን ለማበረታታትና ለማሳደግ መንግስት አስፈላጊውን ሁሉ እያከናወነ ይገኛል ሲሉ አረጋግጠዋል።

‎የብሄራዊ ደም ባንክ ደምና ህብረ ህዋስ ምክትል ዳይሬክተር ወ/ሮ ጤናዬ ደስታ፤ ደም መለገስ የመልካምነት ማሳያ በመሆኑ ደም በመለገስ የሰውን ህይወት መታደግ እንደሚያስፈልግ ተናግረው ከደም የሚገኘውን መድሀኒት ሀገር ውስጥ በማምረት በጤናና በኢኮኖሚ ላይ የሚደርሰውን ጫና መታደግ እንደሚያሻ አብራርተዋል።

‎በሀገራችን 55 የደም ባንኮች እንደሚገኙና ከእነዚህም መካከል 5ቱ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል እንደሚገኙ ያብራሩት ዳይሬክተሯ፤ እነዚህን ባንኮች ከማጠናከር ባሻገር አስፈላጊውን ደም ማሰባሰብ እንዲቻል ሁሉም ርብርብ ሊያደርግ ይገባል ብለዋል።

‎ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን