የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚ የተሻለ ለማድረግ በትኩረት መሰራት እንደሚገባ የዳውሮ ዞን ዋና አስተዳደር ገለፀ

የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚ የተሻለ ለማድረግ በትኩረት መሰራት እንደሚገባ የዳውሮ ዞን ዋና አስተዳደር ገለፀ

‎የዞኑ እና ወረዳ አመራሮችን ያሳተፈ የቀጣዩ የክረምት ወቅት የትኩረት ተግባራት ዙሪያ የውይይት መድረክ ተካሂዷል፡፡

የዳውሮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ገበየሁ በመድረኩ እንዳሉት፤ በገጠር ልማት ስራ ያሉትን መልካም ተግባራት ይበልጥ ለማሳደግ መስራት ያስፈልጋል።

‎የኮሪደር ስራዎችን እያሳለጥን ከዚህ ጎን ለጎን ደግሞ የአርሶ አደሮችን ኢኮኖሚ ይበልጥ ለማሳደግ በዘርፉ ተግባሮች ላይ ርብርብ ማድረግ ይገባል ሲሉ ዋና አስተዳዳሪው አጽንኦት ሰጥተዋል።

‎የገጠር ኮሪደር ልማት የመንገድ መሠረተ ልማት ስራ ብቻ ሣይሆን የአርሶ አደሩን የአኗኗር ሁኔታ ጭምር መቀየር የሚችል እንደሆነ የዞኑ ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ህብረት ስራ ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ በየነ በተላ ተናግረዋል።

‎እንደ ሃላፊው ገለጻ፤ በዞኑ የሚገኙት አርሶ አደሮች ከገጠር ኮሪደር ልማት ጎን ለጎን ከ15 እስከ 20 ዶሮዎች፣ አራት የሚታለቡ ጥገት ላሞች፣ በጓሮ ቢያንስ መቶ የተተከሉ እንሰቶች፤ ሃምሣ ሙዝ ተክልና ከሙዝ ውጪ ፍራፍሬና አትክልት እንዲሁም 250 እግር ቡና መኖር እንዳለበት አቶ በየነ አጽንኦት በመስጠት ተናግረዋል።

‎የገጠር ኮሪደር ልማት የታቀደውን ያክል ግብ እንዲመታ የግብርና ልማት ባለሙያዎች ሚና ትልቅ መሆኑን የመምሪያ ሃላፊው አስታውቀዋል።

‎በአጠቃላይ ለገጠር ኮሪደር ልማት የአርሶ አደሩ የኑሮ ዘይቤን እንዲቀይር በየደረጃው ያሉት አመራሮች መረባረብ እንዳለባቸው በመድረኩ ተነስቷል።

‎በውይይት መድረኩም የዞን አመራር አካላት እና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮች ተሣትፈዋል።

‎ዘጋቢ፡ አሸናፊ ግዛው – ከዋካ ጣቢያችን