በጎፋ ዞን ሣውላ ከተማ ያጋጠመውን የለውጥ መንገድ ችግር ለመቅረፍ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ

በሣውላ ከተማ የሚገኘው የወንባ ወንዝ ብረት ድልድይ በሶዶ ዲንኬ ሣውላ ሸፊቴ መንገድ ስራ ምክንያት መነሳቱን ተከትሎ በህብረተሰቡ ላይ የተፈጠረውን እንግልት ለመቀነስ የተለዋጭ መንገድ ስራ በመጠናቀቅ ላይ ነው።

የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ የድልድዩን ስራ በጎበኙበት ወቅት እንዳሉት በወንባ ወንዝ ድልድይ ላይ የሚደረገው እንቅስቃሴ በመቋረጡና ተለዋጭ መንገድ ባለመኖሩ ከፍተኛ የትራፊክ መጨናነቅ በመፈጠሩና ህብረተሰቡም ላልተፈለገ እንግልት መዳረጉን ተከትሎ ክረምት ከመግባቱ አስቀድሞ የብረት ድልድይ የመግጠም ስራ እየተሰራ ይገኛል።

በወንዙ ላይ ተለዋጭ ድልድይ መሰራቱ አነስተኛና መካከለኛ ተሽከርካሪዎችን ጨምሮ ህብረተሰቡ በእግሩ ለመንቀሳቀስም ጭምር መፍትሔ መሆኑን ዋና አስተዳዳሪው አንስተዋል።

ይህን ተከትሎ በአካባቢው የተፈጠረውን ውጣ ውረድ ለማስቀረት የግንባታ ሂደቱ ተጠናቆ ብረት የመገጣጠም ስራ ብቻ መቅረቱን ጠቅሰው የመግጠሙን ስራ በአንድ ሳምንት ለማጠናቀቅ እየተሰራ ስለመሆኑ ገልጸዋል።

ዘጋቢ፡ አይናለም ሰለሞን – ከሳውላ ጣቢያችን