በኢንቨስትመንት መስክ ከቢሮክራሲ የጸዳ ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት ባለሀብቱን መሳብ እንደሚገባ የይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር ገለጸ

በከተማው የተፈጠረውን ምቹ አጋጣሚ ተጠቅመው እየሠሩ እንደሚገኝ በዘርፉ የተሰማሩ አልሚዎች ተናግረዋል።

ኢንቨስትመንትን ለማበረታታት የባለሀብቶች የኢንቨስትመንት ፎረም በማቋቋም እየሠሩ እንደሚገኝ የገለጹት የይርጋጨፌ ከተማ ከንቲባ አቶ ታደለ ጥላሁን፤ ለኢንቨስትመንት ዋነኛ ጉዳይ የአገልግሎት አሰጣጡን ቀልጣፋነትና ከቢሮክራሲ የጸዳ ማድረግ ነው ብለዋል።

የሚሠሩ ግንባታዎችን ኮሚቴ አዋቅረው ታች በመውረድ የድጋፍና ክትትል ሥራዎች እየተሠሩ እንዳሉም ተናግረዋል።

በኢንቨስትመንቱ መስክ መሰማራት የሚፈልግ ማንኛውም ባለሀብት አስፈላጊው ሁሉ ድጋፍ እንደሚደረግ የገለጹት ከንቲባው፤ በኢንቨስትመንቱ ከተማዋን ከማልማት ባለፈ ለራስ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ጠይቀዋል።

የይርጋጨፌ ከተማ ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ጽ/ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ ዳዊት ታምራት፤ በከተማዋ ከሠላሳ በላይ ኢንቨስተሮች በግንባታው ተሰማርተው እያለሙ መሆናቸውን ጠቅሰው ሌሎችም ሲመጡ በተገቢው ማስተናገድ እንደሚገባና ኢንቨስትመንቱ ሙሉ እንዲሆን የጌጠኛ ድንጋይ፣ የኮሪደርና የአረንጓዴ ስፍራዎች ልማት እየተሠሩ እንዳሉ ገልጸዋል።

አቶ ዮሴፍ ኡዶ፣ ኤርሚያስ ሌሲዎንና ሌሎችም በሁለገብ የገበያ ማዕከል፣ በሆቴል፣ በሞቴልና የኤክትሪክ መኪና ቻርጅ ማድረጊያ የተሰማሩና በሂደት ላይ ያሉ አልሚዎች ናቸው። በከተማዋ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የታየው የኢንቨስትመንት መነቃቃት ይበል የሚያሰኝ እንደሆነም አስረድተዋል።

ዘጋቢ: ውብሸት ካሣሁን – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን