ኮሌጁ በመካከለኛ ደረጃ የሰለጠነ የሰው ሀይልን ለማፍራት ባለፉት ዓመታት ባደረገው ጥረት አበረታች ለውጥ ማስመዝገብ መቻሉን የቡታጅራ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ አስታወቀ

ኮሌጁ ለዘርፉ ስኬታማነት በየደረጃው በሚያደርገው እንቅስቃሴ የባለድርሻ አካላት ድጋፍና ተሳትፎ ተጠናክሮ እንዲቀጥልም ጥሪ አቅርቧል።

የቡታጅራ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ ዲን አቶ አብድልዋሂድ መሐመድ ከደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ወልቂጤ ቅርንጫፍ ጣቢያ በነበራቸው ቆይታ እንዳሉት፤ ኮሌጁ በመካከለኛ ደረጃ የሰለጠነ የሰው ሀይልን ለማፍራት ሰፊ ጥረት እያደረገ ነው።

በዚህም ባለፉት ዓመታት ባደረገው ጥረት ከጊዜ ወደ ጊዜ አበረታች ለውጥ ማስመዝገብ መቻሉን አስረድተዋል።

ኮሌጁ ከተመሠረተ 26 ዓመታትን እንዳስቆጠረ አውስተው፤ በትምህርትና ስልጠና፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን እና በሌሎችም የማህበረሰቡን ችግር በሚፈቱ ተግባራት ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን የተጠናከረ ስራ መስራቱን ተከትሎ በ2011 ዓ.ም ወደ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅነት ማደጉን ተናግረዋል።

በየደረጃው የሚገኙ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ የኮሌጁን የቅበላ ሽፋንን ለማሳደግ በቅንጅት እንደሚሰራ ገልፀው የትምህርትና ስልጠና ስራው ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆንም በጥናት ላይ የተመሠረተ ድጋፍና ክትትል የሚያደርጉ በመሆኑ አበረታች ውጤት መመዝገቡን አስታውቀዋል።

ኮሌጁ በባለፉት 26 ዓመታት ጉዞው ከ30 ሺህ በላይ ዜጎችን የሙያ ባለቤት ማድረግ መቻሉን ጠቁመው፤ አሁን ላይ በመደበኛው መርሃ-ግብር ከ1 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ከደረጃ 1 እስከ እስከ ደረጃ 5 ገበያ መርና ወቅቱን በሚመጥኑ የተለያዩ የስልጠና ዘርፎች ላይ እያሰለጠነ እንደሚገኝ ነው አቶ አብድልዋሂድ ያመላከቱት።

የትምህርትና ስልጠና ስራው ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆን በቀጣይም የተጠናከረ ስራ እንደሚሰራ በመጥቀስ ለዘርፉ ስኬታማነትም ባለድርሻ አካላት እያደረጉት ያለው ድጋፍና ተሳትፎ አበረታች በመሆኑ አጠናክረው እንዲቀጥሉ አስገንዝበዋል።

ዘጋቢ፡ መሐመድ ሽሁር – ከወልቂጤ ጣቢያችን