የኮንታ ዞን የሚዲያና ኮሙኒኬሽን አመራሮችና ባለሙያዎች የውይይት መድረክ በአመያ ከተማ እየተካሄደ ነው

የኮንታ ዞን የሚዲያና ኮሙኒኬሽን አመራሮችና ባለሙያዎች የውይይት መድረክ በአመያ ከተማ እየተካሄደ ነው

ሀዋሳ፡ ግንቦት 13/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) “የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ሚና ለሁለንተናዊ ብልፅግና!” በሚል መሪ ቃል በኮንታ ዞን የሚገኙ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን አመራሮችና ባለሙያዎች የውይይት መድረክ በአመያ ከተማ እየተካሄደ ነው፡፡

በመድረኩ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የዞኑ ረዳት የመንግስት ተጠሪ አቶ ባሻ በላቸው፤ በሀገራችን ባለፉት 7 የለውጥ ዓመታት በርካታ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ውጤቶች ተመዝግበዋል ብለዋል።

በሂደቱም በርካታ ፈተናዎች ማጋጠም ቢችሉም መሻገር ተችሏል ያሉት አቶ ባሻ፤ ለውጤቱም የሚዲያና ኮሙኒኬሽን አካላት ሚና የጎላ እንደነበር አንስተዋል።

በኮንታ ዞን ደረጃም ዞኑ ከተደራጀ ወዲህ ከፍተኛ የሆኑ ለውጦች መታየታቸውን በመጠቆም ይህም በሚዲያ ሲደገፍና ሲተዋወቅ እንደነበርና ተጠናክሮ ሊመራ እንደሚገባም ገልጸዋል።

በኢትዮጵያ የብልጽግና ጉዞ ውስጥ የሚዲያ እና ኮሙኒኬሽን ሚና እና ቀጣይ አቅጣጫዎች በሚል ርዕስ የተዘጋጀውን ሀገራዊ ሰነድ በዞኑ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ ኃላፊ አቶ አበበ ጎበና ቀርቦ ውይይት እየተደረገበት ይገኛል።

በመድረኩ የዞን፣ የወረዳዎችና የከተማ አስተዳደር የመንግስት ኮሙኒኬሽን አመራሮችና ባለሙያዎች እንዲሁም የየመምሪያዎች የመንግስት ኮሙኒኬሽን ፎካል ፐርሰን በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።

ዘጋቢ፡ ፋስካ ሙሉጌታ – ከዋካ ጣቢያችን