ሀዋሳ፡ ግንቦት 03/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) እየተገነቡ ያሉ የጤና ተቋማት የህብረተሰቡን ፍላጎት የሚያሟሉና ለአገልግሎት አሰጣጥ ምቹ ሊሆኑ እንደሚገባ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳደር ዶክተር ኢንጅነር ነጋሸ ዋጌሾ አሳሰቡ፡፡
በርዕሰ መስተዳደሩ የተመራ ልዑክ በካፋ ዞን ገዋታ ወረዳ እየተገነባ ያለውን የቆንዳ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ጎብኝቷል፡፡
የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር ዶክተር ኢንጅነር ነጋሸ ዋጌሾ በዚህ ጊዜ እንደገለጹት የጤና መሰረተ ልማትን ለማስፋት በክልል ደረጃ የጤና ተቋማት ግንባታ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የቆንዳ ሆስፒታል የዚሁ ተግባር አንዱ ማሳያ መሆኑን ገልጸው፥ ግንባታው በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ ተቋራጩ እያደረገ ያለውን ጥረት አጠናክሮ እንዲያስቀጥል አሳስበዋል፡፡
ሆስፒታሉ ተጠናቆ በአፋጣኝ አገልግሎት እንዲስጥ የክልሉ መንግስት ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል፡፡
በግንባታ ሂደት የሚያጋጥሙ ክፍተቶችን የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊዎች ለማስተካከል በሚወስዳቸው እርምጃዎች ላይ የክልሉ መንግስት ድጋፍ እንደማይለይ ገልጸዋል፡፡
የገዋታ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አርጋው ሀይሌ በወረዳው 4 ጤና ጣቢያዎችና 31 ጤና ኬላዎች እንደሚገኙ ገልጸው የቆንዳ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ግንባታ 98 በመቶ መድረሱን ተናግረዋል፡፡
በጉብኝቱ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደርና የግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ማሰረሻ በላቸው፣ የክልሉ ብልጽግና ፖርቲ የአደረጃጀት ዘርፍ ሀላፊ አቶ በላይ ተሰማ እና ሌሎች የክልልና የዞን ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ብዙአየሁ ጫካ – ከቦንጋ ጣቢያችን

More Stories
የግል እና የጋራ መጸዳጃ ቤቶችን በተገቢው በመጠቀም ተላላፊ የሆኑ በሽታዎችን አስቀድሞ መከላከል እንደሚገባ በጉራጌ ዞን የእኖር ወረዳ ጤና ጥበቃ ጽህፈት ቤት አስገነዘበ
12 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በተቋማት የድርጊት መርሐ-ግብርና በፀደቀላቸው በጀት መሠረት ማሰራጨቱን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ፋይናንስ ቢሮ አስታወቀ
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) በምስራቅ ጉራጌ ዞን ቡኢ ከተማ አስተዳደር እየተገነባ የሚገኘውን ብሉ ኤለፋንት ፋይበር ቦርድ ካምፓኒ ጎበኙ