ሀዋሳ፡ ግንቦት 03/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) እየተገነቡ ያሉ የጤና ተቋማት የህብረተሰቡን ፍላጎት የሚያሟሉና ለአገልግሎት አሰጣጥ ምቹ ሊሆኑ እንደሚገባ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳደር ዶክተር ኢንጅነር ነጋሸ ዋጌሾ አሳሰቡ፡፡
በርዕሰ መስተዳደሩ የተመራ ልዑክ በካፋ ዞን ገዋታ ወረዳ እየተገነባ ያለውን የቆንዳ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ጎብኝቷል፡፡
የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር ዶክተር ኢንጅነር ነጋሸ ዋጌሾ በዚህ ጊዜ እንደገለጹት የጤና መሰረተ ልማትን ለማስፋት በክልል ደረጃ የጤና ተቋማት ግንባታ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የቆንዳ ሆስፒታል የዚሁ ተግባር አንዱ ማሳያ መሆኑን ገልጸው፥ ግንባታው በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ ተቋራጩ እያደረገ ያለውን ጥረት አጠናክሮ እንዲያስቀጥል አሳስበዋል፡፡
ሆስፒታሉ ተጠናቆ በአፋጣኝ አገልግሎት እንዲስጥ የክልሉ መንግስት ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል፡፡
በግንባታ ሂደት የሚያጋጥሙ ክፍተቶችን የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊዎች ለማስተካከል በሚወስዳቸው እርምጃዎች ላይ የክልሉ መንግስት ድጋፍ እንደማይለይ ገልጸዋል፡፡
የገዋታ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አርጋው ሀይሌ በወረዳው 4 ጤና ጣቢያዎችና 31 ጤና ኬላዎች እንደሚገኙ ገልጸው የቆንዳ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ግንባታ 98 በመቶ መድረሱን ተናግረዋል፡፡
በጉብኝቱ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደርና የግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ማሰረሻ በላቸው፣ የክልሉ ብልጽግና ፖርቲ የአደረጃጀት ዘርፍ ሀላፊ አቶ በላይ ተሰማ እና ሌሎች የክልልና የዞን ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ብዙአየሁ ጫካ – ከቦንጋ ጣቢያችን

More Stories
የፀረ-ተህዋስያን መድኃኒቶች በጀርሞች መላመድን ለመከላከል በሚደረገው አገራዊ ጥረት ውስጥ የሚዲያ ባለሙያዎች ግንባር ቀደም ሚና ሊጫወቱ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ገለጸ
መምህራን የሚገባቸውን ጥቅማ ጥቅምና መብት በማስጠበቅ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መምህራን ማህበር አስታወቀ
የልማትና መልካም አስተዳደር ተግባራትን ለማፋጠን ግብር ከፋዩ የሚጠበቅበትን ታክስ በወቅቱና በታማኝነት መክፈል እንዳለበት ተገለጸ