በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ንግስት እሌኒ መሐመድ መታሰቢያ ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የ2017 ዓ.ም የተገልጋይ ውይይት መድረክ በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ነው

በሆስፒታሉ የአገልግሎት መስጫ አካባቢዎች የመስክ ምልከታም ተደርጓል።

በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የንግስት ኢሌኒ መሐመድ መታሰቢያ ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ቺፍ ኤክስኪዩቲቭ ዳይሬክተር ዶ/ር ይድነቃቸው ደዳቸው በመግቢያ ንግግራቸው ወቅት እንደገለፁት፤ ሆስፒታሉ በሰብ ስፔሻሊቲና ስፔሻሊቲ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል።

ይሁን እንጂ አልፎ አልፎ ከዚህ ቀደም ከህብረተሰቡ የሚነሱ የተለያዩ የአገልግሎት ችግሮች ይስተዋሉ እንደነበር አንስተው፤ የሆስፒታሉ የማኔጅመንት አባላት ባደረጉት የጋራ ርብርብ ዘርፈ ብዙ ለውጦች እየታዩ መጥተዋል ብለዋል።

ውይይቱ ያሉብንን ጉድለቶች በመሸፈን ለተገልጋዮች ተገቢውን የህክምናና አስፈላጊ አገልግሎቶችን ተደራሽ በማድረግ የህብረተሰቡን እርካታ ለማሳደግ ጉልህ አስተዋፅኦ ያለው መሆኑን አመላክተዋል።

በውይይት መድረኩ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማቴዎስ አኒዮ፣ የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት ዶ/ር ዳዊት ሃዬሶና የዩኒቨርሲቲው የማኔጅመንትና የሴኔት አባላትን ጨምሮ የዞንና የክልል ባለድርሻ አካላትና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እየተሳተፉ ይገኛል።

በውይይቱም ህብረተሰቡን የሚያረካ ተገቢውን የህብረተሰብ አገልግሎት ተደራሽ ማድረግ በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙሪያ የጋራ ግንዛቤ እንደሚያዝ ይጠበቃል።

ዘጋቢ: አማኑኤል አጤቦ – ከሆሳዕና ጣቢያችን