በደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት ኮንትሮባንድና ህገ-ወጥ ንግዶች እየጨመሩ መምጣታቸውን የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ አስታወቀ

ኮንትሮባንድንና ህገ-ወጥ ንግዶችን ለመከላከል የሚያስችል የትብብር መድረክ በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሂዷል።

ኮንትሮባንድና ህገ-ወጥ ንግዶች የሀገርን ኢኮኖሚ ብሎም ህጋዊ የንግድ ስርአቱን ክፉኛ እየጎዱ እንዳሉ ይነገራል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ሰናይት ሰለሞን መድረኩን በንግግር ሲከፍቱ እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ በኢኮኖሚዋ ላይ ከፍተኛ ጫና የፈጠረውን ህገ-ወጥ ንግድን ለመከላከል በርካታ ጥረቶችን እያከናወነች ትገኛለች።

በክልሉም ኮንትሮባንድና ህገ-ወጥ ንግዶች እየተባባሱ መምጣታቸው የሚናገሩት ወ/ሮ ሰናይት፤ ይህም በህዝቡ ጤና ላይ ከፍተኛ ጫና እየፈጠረ መምጣቱንም የቢሮ ኃላፊዋ አውስተዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ በንቅናቄ መድረኩ ላይ ተገኝተው እንደተናገሩት፤ በክልሉ የፀጥታ ችግር ከሆኑ ጉዳዮች አንዱ ኮንትሮባንድና ህገ-ወጥ ንግዶች የሀገሪቱን የብልፅግና ጉዞን የሚያደናቅፉ ናቸው።

የኮንትሮባንድና ህገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ወደአልተፈለገ አቅጣጫ እንዲጓዝ እያደረገ መሆኑን ያስታወሱት ርዕሰ አስተዳደሩ፤ በህገ-ወጥ ንግዱ ጥቂቶች ብቻ የሚከብሩበት ስለመሆኑ አንስተዋል።

በይበልጥ የግብርና ምርቶች በክልሉ በህገ-ወጥ መንገድ ወደአጎራባች ሀገራት እየገቡ መሆናቸውን የተናገሩት አቶ ጥላሁን፤ ይህን ተግባር በቅንጅት መግታት ያስፈልጋልም ብለዋል።

በክልሉ ህገ-ወጥ የጦር መሣሪያ መኖሩን የጠቆሙት አቶ ጥላሁን፤ ይህም የክልሉን ሠላምና ደህንነት አደጋ ላይ እንዳይጥለው ጥንቃቄ ሊወሰድ ይገባልም ብለዋል።

ለህዝብ ጤና ስጋት የሆኑ የመዳኃኒትና ምግብ ነክ የሆኑ ህገ-ወጥ ኮንትሮባንድ እንቅስቃሴዎችን በመረጃ በመደገፍ የመከላከል ስራውን ማጠናከር ይገባል ብለዋል።

ዘጋቢ: በኃይሉ ሙሉጌታ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን