ከ5 መቶ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሮች እየተሰራጨ መሆኑ ተገለጸ

“ሚሲሚዶ እና ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ” የተሰኙ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ለኮሬ ዞን ግብርና መምሪያ የምርጥ ዘር ድጋፍ ማድረጋቸው ተገልጿል።

የኮሬ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ እና የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አስታረቀኝ አንደባ እንደገለጹት፤ ሁለቱ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ያደረጉት የምርጥ ዘር ድጋፍ ለዚህ ዓላማ መንግሥት ያወጣ የነበረውን ወጪ ያስቀረ ነው።

በጥራትና በአቅርቦት መጠን ከአምናው የተሻለና ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሮች መሰራጨቱንም የኮሬ ዞን ግብርና መምሪያ አስታውቋል።

የኮሬ ዞን ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት አስተባባሪ አቶ አሸናፊ አሳምነው፤ ከሁለቱም ድርጅቶች የተገኘውን ምርጥ ዘር በዞኑ ስር ለሚገኙ ሁለቱ ወረዳዎች እና ከተማ አስተዳደር በማቅረባቸው በቀጥታ ለአርሶአደሮች በማሰራጨት ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል።

ከሁለቱም ድርጅቶች የተገኘው ድጋፍ ከምርጥ ዘር አቅርቦት ጋር ሲያጋጥማቸው የነበረውን ችግር የፈታ መሆኑን የተናገሩት አቶ አሸናፊ፤ 2 መቶ 65 ኩንታል የበቆሎ ምርጥ ዘር እና 2 መቶ 12 ኩንታል ቦሎቄ በድምሩ 5 መቶ 40 ኩንታል የበቆሎ እና ቦሎቄ ምርጥ ዘር 75 በመቶ ያህሉን ለአርሶ አደሮች ማሰራጨታቸውን ገልጸዋል።

አርሶአደር ኢሳያስ ሎካ በኮሬ ዞን ሳርማሌ ወረዳ የጉሙሬ ቀበሌ ነዋሪ ሲሆኑ ከአምናው የተሻለ ምርጥ ዘር በተመጣጣኝ ዋጋ በማግኘታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል።

ዘጋቢ: ተሾመ ፀጋዬ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን