ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የአፈር ማዳበሪያ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑ ተገለጸ
ከ12 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሮች ማሰራጨቱን የኮሬ ዞን ግብርና መምሪያ አስታውቋል።
የኮሬ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አስታረቀኝ አንደባ፤ ምርታማነትን ከመጨመር ረገድ የአፈር ማዳበሪያ ወሳኝነት እንዳለውና ዘንድሮ ለበልግ እርሻ የሚውል ከ12 ሺህ ኩንታል በላይ ለአርሶአደሮች በማቅረብ ላይ እንደሚገኙ ገልፀዋል።
የሰብል ልማት ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ አሸናፊ አሳምነው በበኩላቸው፤ በዞን ደረጃ የቀረበውን የአፈር ማዳበሪያ ለወረዳዎች ማድረሳቸውንና አሁን ላይ ወረዳዎች ለአርሶ አደሮች በማሰራጨት ላይ እንደሚገኙ አስረድተዋል።
ከክልል ለዞን የተላከው 7 ሺህ 2 መቶ ኩንታል ዳፕ እና 4 ሺህ 8 መቶ ኩንታል ዩሪያ በድምሩ 12 ሺህ ኩንታል መቅረቡን የገለጹት አስተባባሪው አሁን ላይ በሁሉም አካባቢዎች ስርጭት እየተደረገ መሆኑንም አስታውቀዋል።
በዞን ደረጃ እስከአሁን ከተሰራጨው ማዳበሪያ ከ11 ሚሊዮን ብር በላይ መሰብሰቡንና ከ8 ሚሊዮን በላይ ገንዘብ ባንክ ገቢ መደረጉን የቡድን መሪው አብራርተዋል።
በማዳበሪያ አጠቃቀም ዙሪያ የአርሶ አደሮቹ ግንዛቤ እየጨመረ ከመምጣቱ የተነሳ አቅርቦቱም በየጊዜው እየጨመረ መምጣቱን የተናገሩት አቶ አሸናፊ፤ ለዚህም የባለሙያዎች ሚና የጎላ እንደሆነ ገልጸዋል።
ከአቅርቦት ውስንነት ጋር ያጋጠመውን ችግር ለመፍታት ከክልሉ ጋር በተያዘው አቅጣጫ መጋዘን ያለው ተሰራጭቶ ሲጠናቀቅ ተጨማሪ ለማስገባት ከስምምነት መድረሳቸውን አስታውቀዋል።
አርሶ አደር ጉይባ ጉንአ እና ትሩፋት ጾካደ በጎርካ ወረዳ የሱሉኮና ሻፉሌ ቀበሌ ነዋሪዎች ሲሆኑ ውስንነቶች ቢኖሩም የአፈር ማዳበሪያው በጊዜ እንደደረሳቸው ገልጸዋል።
ዘጋቢ፡ ተሾመ ፀጋዬ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
በክልሉ የሚገኙ ነዋሪዎችን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል ሥራ በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ገለጹ
የእናቶችንና ጨቅላ ህፃናትን ሞት ለመቀነስ በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርእሰ መስተዳደር (ዶ/ር ) እንዳሻው ጣሰው በተገኙበት በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ምርቃትና የመሰረተ ድንጋይ የማስቀመጥ ስነ-ስረዓት እየተካሄደ ይገኛል