የፌደራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀነራል ዳመነ ዳሮታ በሚዛን ማረሚያ ተቋም ተገኝተው ከታራሚዎች ጋር የ2016 የዘመን መለወጫ በዓልን በጋራ አከበሩ

የፌደራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀነራል ዳመነ ዳሮታ በሚዛን ማረሚያ ተቋም ተገኝተው ከታራሚዎች ጋር የ2016 የዘመን መለወጫ በዓልን በጋራ አከበሩ

የህግ ታራሚዎችም የፌደራልና የክልል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነሮች እና ከፍተኛ የመንግስት አመራሮች ጋር የዘመን መለወጫ በዓልን ማክበራቸው እንዳስደስታቸው ገልፀዋል።

የፌደራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን የታራሚዎች ሰብኣዊ መብት አጠባበቅና አያያዝ በማረም ማነፅ አገለግሎትና በመሠረታዊ ፍላጎት እንዲሁም በአስተዳደር ጉዳዮች በተከናወኑ ተግባራት ለውጥ እየተመዘገበ መምጣቱ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የሁሉም ኃላፊነት መሆኑን መረዳት እንደሚገባ የፌደራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀነራል ዳመነ ዳሮታ ተናግረዋል።

በተለይም የዕድገታችን ጎታች የሆነው በዘርና በጎሳ መቃቃር በሃይማኖት አለመግባባትን በመዋጋት በህዝብና በመንግስት የተጣለብንን ኃላፊነት ልንወጣ ይገባናል ያሉት ኮሚሽነር ጀነራል ዳመነ ዳሮታ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በሚዛን ማረሚያ ተቋም ተገኝተው የዘመን መለወጫ በዓልን ከታራሚዎችና ከባለድርሻ አካላት ጋር ማክበራቸው እንዳስደስታቸው ገልጸዋል።

በማወቅም ሆነ ባለማወቅም ወንጀል ፈፅመው የፍርድ ቤት ውሳኔ አግኝተው በማረሚያ ተቋም በመታረም ላይ ከሚገኙት የህግ ታራሚዎች ጋር የዘመን መለወጫ በዓልን ማክበራቸው እንዳስደሰታቸውና ትልቅ በረከት መሆኑን የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳደሪ ተወካይና የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ልዩ አማካሪ አቶ ተስፋዬ ጊስካር ተናግረዋል።

የሚዛን ማረሚያ ተቋም ኃላፊ ኢንስፔክተር ጌትነት ፍቃዱ የህግ ታራሚዎች ሰብኣዊ መብታቸው እንዲጠበቅና መሠረታዊ ፍላጎታቸው እንዲሟላ ከማድረግም ባሻገር በአመለካከትና በአስተሳሰብ ተለውጦ አምራች ዜጋ እንዲሆኑ ተቋሙ እየሠራ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የዘመን መለወጫ በዓልን ከእንግዶች ጋር ማክበራቸው ደስታዬ ከፍ ያለ ነው ብለዋል።

የማረሚያ ተቋሙ የጥበቃ ደህንነት ስምሪት ፍተሻ ድጋፍ ኃላፊ ሳጅን አሰፋ ዕድሉ እና የግብርና ባለሙያ ወይዘሮ ማረታ ሀይመሎ ከፌደራል ማረሚያ ቤት ከፍተኛ አመራሮች ከታራሚዎች ጋር በዓሉን በቤተሰባዊነት እያከበሩ መሆናቸውን ተናገረዋል።

ካነጋገርናቸው የህግ ታራሚዎች መካከል የህግ ታራሚ ተወካይ ደረጀ ግዥ፣ ታደለ ገረመው፣ ጀግና ተፈራ እና የህግ ታራሚ ዘማች ኪዳነ በበኩላቸው የፌደራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀነራል ዳመነ ዳሮታ እና የልዑክ ቡድናቸው በማረሚያ ተቋም ተገኝተው የዘመን መለወጫ በዓልን በጋራ ማክበራቸው እንዳስደሰታቸው ገልፀዋል።

ዘጋቢ፡ አብዲሳ ዮናስ – ከሚዛን ጣቢያችን