በቡታጅራ ከተማ ቢሮዎች ዝግጁ ሆነዋል
ሀዋሳ: ጳጉሜ 03/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) በቡታጅራ ከተማ የተመደቡ ክላስተር መሥሪያ ቤቶች የቢሮ ዝግጅት መደረጉን የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ሙስጠፋ ሀሰን ገለፁ::
ጳጉሜ 04 ቀን 2015 ዓ.ም የሥራ ማስጀመሪያ መርሀግብር እንደሚከናወንም ተገልጿል::
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የማዕከል ከተማ ከሆኑት አንዷ የሆነችው የቡታጅራ ከተማ አስፈላጊ ቅድመ ዝግጅቶችን ማጠናቀቋን የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ሙስጠፋ ሀሰን ተናግረዋል::
ከደሬቴድ ጋር ቆይታ ያደረጉት ምክትል አስተዳዳሪው ከተማው የክላስተር ከተማ ሆና መመረጧ ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች ያሉት ነው ብለዋል:: ይህም ከሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ከገበያ ትስስር እና ከኢንቨስትመንት አንፃር ትልቅ አስተዋጽኦ ያበረክታል ነው ያሉት::
ከተማዋ ለእንግዶች ምቹ ትሆን ዘንድ ከከተማ ፅዳት ጀምሮ እስከ ቢሮ ዝግጅት ያሉ ተግባራት መከናወናቸውን አስታውቀዋል:: ይህን ተከትሎ ጳጉሜ 04 ቀን 2015 ዓ.ም ከፍተኛ የክልሉ የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ይፋዊ የሥራ ማስጀመሪያ መርሀግብር ይካሄዳል::
የቢሮ ኃላፊዎች በቀጥታ ወደ ሥራ በመግባት የተሰጣቸውን የህዝብና የመንግስታ ኃላፊነት ያለምንም ችግር ይወጡ ዘንድ ምቹ ሁኔታዎችን የመፍጠር ሥራ መሠራቱን አቶ ሙስጠፋ ገልጸዋል::
ከከተማዋ ባለሀብቶች ጋር በመነጋገር ለኃላፊዎቹ ለ6 ወር በነፃ የሚኖሩበት የመኖሪያ ቤት ተዘጋጅቷል ብለዋል:: ባለሀብቱ ላሳየው በጎ ፈቃደኝነት ምስጋና አቅርበዋል::
ወደ ከተማዋ ተመድበው የሚመጡ የመንግስት ሠራተኞችም ባይተዋርነት ሳይሰማቸው እንደ ቤታቸው ሆነው እንዲኖሩ የሚያስችል ሥራ ከህብረተሰቡ ጋር ተሰርቷል ብለዋል::
እድገት በጊዜ ሂደት የሚመጣ መሆኑን ህብረተሰቡ ተገንዝቦ ለእንግዶች በተመጣጣኝ ዋጋ የመኖሪያ ቤት ማከራየት መልካም መሆኑን አንስተዋል::
በአራቱ ቢሮዎች ተመድበው ወደ ከተማዋ ለሚመጡ የመንግስት ሠራተኞች በማህበር በማደራጀት የመኖሪያ ቤት እድል ተጠቃሚ እንዲሆኑም ቅድሚያ ተሰጥቶ እንደሚሠራ አብራርተዋል::
ዘጋቢ: ማሬ ቃጦ
More Stories
በሀሳብ ልዕልና የሚያምን የፖለቲካ ሥነ-ምህዳርን በማስፋት ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በመመካከርና በመደጋገፍ መስራት እንደሚገባ ተገለጸ
የኢፌዲሪ ውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ የከርሰ ምድር ውሃ ፕሮጀክት ከ82 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ በጉራጌ ዞን ምሁር አክሊል ወረዳ መቆርቆር ቀበሌ ያስገነባው የንጹህ መጠ ውሃ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆነ
የኡዱሂያ የዕርድ ስርዓት….የአብሮነት ነፀብራቅ