አርሰናል የውድድር ዓመቱን የመጀመሪያ ሽንፈት አስተናገደ!

 አርሰናል የውድድር ዓመቱን የመጀመሪያ ሽንፈት አስተናገደ!



በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ 5ኛ ሳምንት መርሃ ግብር የወቅቱ ሻምፒዮን አርሰናል ከሜዳው ውጪ ከብራይተን ጋር ባደረገው ጨዋታ የጠበቀውን ውጤት ሳያገኝ ቀርቷል።



125ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን በድምቀት እያከበረ የሚገኘው አስተናጋጁ ብራይተን ብልጫ ወስዶ በመጫወት 3 ለ 0 በሆነ ሰፊ ውጤት አርሰናልን ረቷል።



በዚህም የሰሜን ለንደኑ ክለብ አርሰናል በአዲሱ የውድድር ዓመት የመጀመሪያ ሽንፈቱን አስተናግዷል።



ለብራይተን የድል ጎሎችን ፓስካል ግሮስ፣ቻራላምፖስ ኮስቱላስ እና ቼማ አንድሬስ አስገኝተዋል።

አርሰናል በፕሪሚዬር ሊጉ ከሶስት ዓመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በአንድ ጨዋታ ሶስት ጎሎች ተቆጥረውበታል።



የሚገርመው ነገር፣ ከሶስት ዓመት በፊትም መረቡ በሶስት ጎሎች የተደፈረው ዛሬ በመድፈኞቹ ላይ 3 ጎሎችን ባስቆጠረው በዚሁ ብራይተን ነበር።



ብራይተን አርሰናልን ማሸነፍ የቻለው ከስድስት ጨዋታዎች በኋላ ነው።

ይህንን ድል ተከትሎ ብራይተን ነጥቡን ወደ 10 ከፍ በማድረግ 3ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል።



ሽንፈት ያስተናገደው አርሰናል በበኩሉ በ12 ነጥብ ላይ የቆመ ሲሆን፤ አንድ ቀሪ ጨዋታ ካለው ማንቸስተር ሲቲ በግብ ክፍያ ተበልጦ መሪነቱን ተነጥቋል።



ዘጋቢ፡ሙሉቀን ባሳ