በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ምርመራ እና ልየታ ተካሄደ‎

‎በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ምርመራ እና ልየታ ተካሄደ

‎የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር በዓለምአቀፍ ደረጃ ከጡት ካንሰር ቀጥሎ ገዳይ በሽታ በመሆኑ ነው በወረዳው ለሚገኙ ሴቶች የምርመራ ዘመቻው የተካሄደው።

‎በጌዴኦ ዞን የይርጋጨፌ ወረዳ ጤና ጥበቃ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ተካልኝ ጥላሁን ከጤና ተቋም ራቅ ያሉ ሴቶች ህክምና እንዲያገኙ ከአጋር ድርጅቶች ጋር በመተባበር የምርመራ እና የልየታ ዘመቻ እያደረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል።

‎በወረዳው ባሉ ሁሉም ቀበሌያት የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር፣ ሲኖግራፊ፣ የደም ግፊት እና የስኳር በሽታዎችን በዘመቻ መልክ በምርመራ የመለየት ሥራ እየሠሩ መሆናቸውንም ኃላፊው አስረድተዋል።

‎ግራውንድስ ፎር ሄልዝ አስተባባሪ አቶ መስፍን ዋና በበኩላቸው፣ የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር በዓለም አቀፍ ደረጃ ከጡት ካንሰር ቀጥሎ ገዳይና አደገኛ በሽታ በመሆኑ ሴቶች በንቃት ተመርምረው ራሳቸውን ማወቅ እንዳለባቸው ገልጸዋል።

‎የአንዲት ሴት ሕይወት ዋጋ ስላላት በማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ላይ ትኩረት አድርገው እየሠሩ መሆናቸውን በመግለጽ ከልየታ በኋላ በጊዜ ህክምና የሚያገኙበት ሁኔታ መመቻቸቱን አስተባባሪው ጠቁመዋል።

‎በወረዳው የቆንጋ ጤና ጣቢያ እና የብርብስ ቄላ ጤና ኬላ ባለሙያዎች ወይዘሮ አበበች ባፋ እና መሠረት ታደሰ እንደተናገሩት፤ የምርመራው ሂደት ቀድሞ ከነበረው የተለየ በመሆኑ በቀላሉ መጨረስ እንደሚቻል ነው የገለጹት።

‎በማህበረሰቡ የግንዛቤ ዕጥረት በመኖሩ ወደ ጤና ጣቢያ በመሄድ እንዲመረመሩ የቅስቀሳ ሥራ እያከናወኑ መቆየታቸውን ያነሱት ባለሙያዎቹ በዚህም በርካታ ሴቶች ተጠቃሚ መሆናቸውን አስረድተዋል።

‎ምርመራ ሲያደርጉ አግኝንተን ያነጋገርናቸው ወይዘሮ ፀሐይነሽ እሸቱ፣ ዘለቀች ባርሳ እና ሌሎችም የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ምርመራ አካባቢያቸው ላይ በመምጣቱ መደሰታቸውን በመግለጽ ምርመራው ራስን በማወቅ ቶሎ ህክምና ለማግኘት እንደሚረዳቸውም ተናግረዋል።


‎ዘጋቢ: አሀዱ አሸናፊ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን