በክልሉ ለተጋላጭ የህብረተሰብ ክፍሎች የተቀናጀ የማህበራዊ ጥበቃና ድጋፍ ስርዓትን ማጠናከር እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ አስታወቀ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ የማህበረሰብ አቀፍ ድጋፍና ክብካቤ ጥምረትና በተጋላጭ ልየታ ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በሳውላ ከተማ ተካሂዷል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ካሴች ኤሊያስ መድረኩን ሲከፍቱ፤ መንግስት የዜጎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ለማቃለል እና ድህነትን ለማስወገድ ህዝቡ በየደረጃው የሚሳተፍበትና የሚጠቀምበት ድሃን ማዕከል ያደረገ፣ ፈጣን፣ ተከታታይ እና ዘላቂ ልማትን ማረጋገጥ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በመደበኛ እና መደበኛ ባልሆነ መንገድ ድህነትን፣ የዜጐችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ስጋት፣ ተጋላጭነትን እና መገለልን ለመቀነስ የሚያስችል እርምጃ በመውሰድ ለሁሉም ተደራሽ የሆነ የተመጣጠነ እድገት ለማረጋገጥ መትጋት ይገባል ብለዋል።
በዋነኝነት በተፈጥሮና በሰው ሰራሽ አደጋ፣ በኢኮኖሚና በማህበራዊ ችግሮች ምክንያት ለከፋ ችግር ተጋላጭ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች በተቀናጀ ሁኔታ ጥበቃ እንዲያገኙ የማድረግ፣ ዜጎች ለተለያዩ ችግሮች እንዳይጋለጡ መከላከል ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል።
የቢሮው ምክትል ኃላፊና የማህበራዊ ዘርፍ ኃላፊ ወ/ሮ ምህረት በላይ በበኩላቸው፤ የማህበራዊ ዋስትና ስርዓትን የመዘርጋት፣ የዜጎችን ሰርቶ የማግኘትና ጥሪት የመያዝ አቅምን የማጎልበት፣ የሥራ ዕድልና የኑሮ ሁኔታን የማሻሻል እና ለጥቃትና በደል ተጋላጭ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን የህግ ጥበቃና ድጋፍ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆን ያስፈልጋል ብለዋል።
ተጋላጮችን መደገፍና ኑሯቸውን ማሻሻል ውጤታማ በሆነ መንገድ ለመፈጸም ከክልል ጀምሮ እስከ ወረዳ ድረስ ይህንን የሚያስተባብር ማህበራዊ ጥበቃ አስተባባሪና ቴክኒክ ኮሚቴ በማቋቋም እና በቀበሌ ደረጃ ደግሞ የማህበረሰብ አቀፍ ድጋፍና ክብካቤ ጥምረት በማደራጀት እንደሚፈጸም አስረድተዋል።
በቀበሌ ማህበረሰብ አቀፍ ድጋፍና ክብካቤ ጥምረት ላይ እና የተጋላጭ ልየታ ላይ በቢሮው የማህበራዊ ችግሮች መከላከል ዳይሬክቶረት አቶ አግዜ ናራዶ እንዲሁም በመረጃ መሰብሰቢያ ፎርማት ላይ በቢሮው የማህበራዊ ጥበቃ ባለሙያ አቶ አመኑ እራሴ ቀርቦ ውይይት ተካሂዷል።
የመድረኩ ተሳታፊዎች ሀሳብና አስተያየት ሰጥተው ከመድረኩ ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቷል።
ዘጋቢ፡ አይናለም ሰለሞን – ከሳውላ ጣቢያችን

More Stories
ማሳቸውን ለመኸር እርሻ ደጋግማው በማረስ አለስልሰው በወቅቱ ለመዝራት መዘጋጀታቸውን በከምባታ ዞን ቀዲዳ ጋሜላ ወረዳ ያነጋገርናቸው አንዳንድ አርሶአደሮች ተናገሩ
በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በተለያዩ የስራ ዘርፎች ከ40 ሺህ በላይ ወጣቶችን ተሳታፊ በማድረግ 46 ሚሊዮን 620 ሺህ ብር በላይ ከመንግሥት ሊወጣ የሚችለውን ለማዳን ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ስፖርት ጽ/ቤት አስታወቀ
የቀቤና ልዩ ወረዳ ማህበረሰብ የልማት ፍላጎት ማሟላት የሚቻለው ግብርና ታክስ በታማኝነትና በወቅቱ መክፈል ሲቻል መሆኑ ተገለጸ