በጎፋ ዞን ወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት የበጋ ማጠቃለያና የክረምት በጎ ስራ ማስጀመሪያ መረሃ-ግብር ተካሄደ

በጎፋ ዞን ወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት የበጋ ማጠቃለያና የክረምት በጎ ስራ ማስጀመሪያ መረሃ-ግብር ተካሄደ

ሀዋሳ፡ ሰኔ 19/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) በጎፋ ዞን ወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት የበጋ ማጠቃለያና የክረምት በጎ ስራ ማስጀመሪያ መረሃ-ግብር በጋልማ ከተማ አካሂዷል፡፡

በክረምቱ ወቅት 148 ሺ ወጣቶችን በማሳተፍ 430 ሺ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የወጣቶችና በጎ ፈቃድ አገልግሎት ጽ/ቤት አስታውቋል።

‎”በጎነት ለኢትዮጵያ ከፍታ” በሚል መሪ ቃል በጎፋ ዞን በዞናዊ የክረምት በጎ ስራ ማስጀመሪያ በአንዲት አቅመ ደካማ እናት የቤት ግንባታ ስራ በጋልማ ከተማ ተጀምሯል።

‎የጋልማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢንጂነር ተስፋለም ነከረ፤ በከተማዋ የአቅመ ደካማና የገቢ አቅም የሌላቸው ግለሰቦች የልየታ ስራ መሰራቱንና በዚህም ክረምት በዞኑ ድጋፍ የአንዲት እናት ቤት ደረጃውን በጠበቀ መልኩ መስራት መጀመሩን ተናግረዋል።

‎የጎፋ ዞን ዋና አስተዳደር ኢጂነር ዳግማዊ አየለ በበኩላቸው፤ የተቸገሩትን መርዳት የኢትዮጵያዊነት ባህላችን ከመሆኑም ባሻገር አብሮ የመበልጸግና የማደግ መርህን መከተል ከፈጣሪ የሚገኝ ትልቅ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል።

‎የመንግስት ተቋማትና ባለሀብቶች፣ ወጣቶችና የሀይማኖት ተቋማት አቅመ ደካማ ወገኖቻችንን መደገፍ ከፈጣሪ የሚሰጥ ጸጋ መሆኑን እንዲሁም፤ የህሊና እርካታን የሚሰጥ ክንውን በመሆኑ ማህበረሰቡ የተለመደውን ትብብር እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።

‎ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍሎች በማሳተፍ በክረምት ወራት ደረጃቸውን የጠበቁ ቤቶች መገንባት እንደሚገባ አሳስበዋል።

‎የጎፋ ዞን ወጣቶችና በጎ ፍቃድ አገልግሎት መምሪያ ኃላፊ አቶ ብረሃኑ ደቻሳ፤ በበጋው ወቅት በ18 የሥራ መስኮች ውጤታማ መሆናቸውን አንስተው በክረምቱ ወቅትም 148 ሺ ወጣቶችን በማሳተፍ 430ሺ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ በማድረግ ከ280 ሚሊየን ብር በላይ የሚሆነውን ወጪ ለማስቀረት መታቀዱን ተናግረዋል፡፡

‎ድጋፍ የተደረገላቸው አቅመ ደካማ እናት የገቢ አቅም እንደሌላቸውና ለረዥም ጊዜ መቸገራቸውን አንሰተው፤ ቤትና የቤት ቁሳቁስ ለሟሟላት ለተደረገው ድጋፍ የዞኑን መንግስት አመስግነዋል፡፡

‎በዕለቱ “አንድም ዜጋ በደም ዕጦት እንዳይሞት በበጎ ፈቃድ ድርሻችን እንውጣ” በሚል መሪ ቃል የደም ልገሳ በማድረግ መረሃ-ግብሩ ተጠናቋል።

‎ዘጋቢ፡ ሰንታየሁ ሙላቱ – ከሳውላ ጣቢያችን