በጎፋ ዞን የክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ማስጀመሪያ ፕሮግራም ተካሄደ

በጎፋ ዞን የክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ማስጀመሪያ ፕሮግራም ተካሄደ

ሀዋሳ፡ ሐምሌ 05/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) በጎፋ ዞን ከ120 ሺህ በላይ ወጣቶች የሚሳተፉበት የክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ማስጀመሪያ ፕሮግራም ተካሂዷል።

የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዶክተር ጌትነት በጋሻው ወጣቶች ያላቸውን ዕምቅ አቅም ተጠቅመው በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ዘርፍ በአካባቢው ልማት በንቃት በመሳተፍ ህብረተሰቡን ማገልገል እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።

ዞኑ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት በሚከናወኑ ተግባራት ላይ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልፀው ተቋማት፣ ባለሀብቶችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል።

የዞኑ ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ አወቀ ዓለሙ በበጋ ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መርሀ ግብር ከፍተኛ ፋይዳ ያላቸውን ተግባራት መከናወናቸውን ገልፀዋል፡፡

በበጋ ወራት የወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ69 ሺህ በላይ ወጣቶች የተሳታፉ ሲሆን 240 ሺህ የሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ በማድረግ h63 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ማዳን መቻሉን ተናግረዋል፡፡

በክረምት የወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት 120 ሺህ 576 ወጣቶችን በማሳተፍ 361 ሺ 728 የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ለማድረግ መታቀዱን አንስተዋል።

አክለውም በአገልግሎቱ 99 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ወጪ ለማደን ታቅዷል ብለዋል።

የመምሪያው ምክትል ኃላፊና የወጣቶች ዘርፍ ኃላፊ አቶ ታደለ ታደሰ ለማህበረሰቡ ከፍተኛ ፈይዳ ባላቸው 11 የተለያዩ የስራ ዘርፎች ወጣቶቹ እንደሚሳተፉ ነው የገለጹት፡፡

በአረንጓዴ አሻራ፣ አረጋውያንን በመደገፍና ቤታቸውን መጠገን፣ በከተማ ጽዳት፣ በደም ልገሳ፣ በማጠናከሪያ ትምህርት፣ በጤናና በሌሎችም መስኮች ይሳተፋሉ ብለዋል።

ወጣት ተመስገን ኡባ እና ወጣት ማሩ ደባልቄ በጋራ እንዳሉት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራ የህሊና እርካታ የሚሰጥ ተግባር በመሆኑ ወጣቶችን በማስተባበር በንቃት ለመሳተፍ መዘጋጀታቸውን አረጋግጠዋል ።

በዕለቱ አቅመ ደካማ የሆኑትን የወ/ሮ ሙተነ ሙሎ ቤት የማደስ ስራ ተሰርቷል።

ዘጋቢ፡ አይናለም ሰለሞን ከሳውላ ጣቢያችን