ኤኮ-ቱሪዝምን በማስፋፋት የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ለመደገፍ በትኩረት እየተሰራ ነው – የጋሞ ዞን ባሕልና ቱሪዝም መምሪያ

ሀዋሳ፡ ሐምሌ 03/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) ኤኮ-ቱሪዝምን በማስፋፋት የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ለመደገፍ እየሰራ መሆኑን የጋሞ ዞን ባሕልና ቱሪዝም መምሪያ አስታወቀ፡፡

የመምሪያ ኃላፊው ተወካይ ወ/ሮ ሰብለወንጌል ከበደ እንዳሉት ወጣቶች በማህበር በመደራጀት በቱሪስት መዳረሻዎች የየአካባቢውን ባሕልና ወግ በማስተዋወቅ በሚያገኙት ራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን እያስተዳደሩ ይገኛሉ፡፡

ዞኑ በርካታ የቱሪስት መዳረሻዎች ያሉ በመሆኑ በአስጎብኚነት የተደራጁ ወጣቶች የአካባቢውን ባሕል፣ ምግብና አመጋገብ እንዲሁም ልብስ በማስተዋወቅ የአካባቢው ባሕል ተጠብቆ እንዲቆይ ያደርጋሉ፡፡

በጋሞ ዞን ባሕልና ቱሪዝም መምሪያ የቱሪዝም መዳረሻዎች አገልግሎቶች ምርቶች ዋና ሥራ ሒደት አስተባባሪ አቶ ገመቹ ቡልቡላ ኤኮ-ቱሪዝም የኤኮ-ሲስተምና የቱሪዝም እንቅስቃሴ ወይም ሁለቱንም ያቀፈ መሆኑን ገልጸው በአግባቡ መጠቀምና መንከባከብ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

በርካታ ቱሪስቶች ሲመጡ በተለያዩ ሆቴሎች፣ ሪዞርቶችና ሎጆች ያርፋሉ፣ ይመገባሉ እንዲሁም የመሳሰሉ ተግባራትን ሲፈጽሙ የአካባቢው ሰዎች ይጠቀማሉ ገቢያቸው ያድጋል መንግስትም ለሚጠቀሙት ቫት ስለሚከፍሉ ይጠቀማል ብለዋል፡፡

በጋሞ ዞን አበረታች የቱሪዝም እንቅስቃሴዎች አሉ፡፡ ዞኑ ተፈጥሯዊ ባሕላዊና ሰው-ሰራሽ መዳረሻዎች ያሉት በመሆኑ ሰፊ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኝ ነው አቶ ገመቹ የተናገሩት፡፡

ኤኮ-ቱሪዝም ተፈጥሮን፣ የነገውን ትውልድ መስረት ያደረገ በመሆኑ መጠበቅና መንከባከብ ያስፈልጋል ያሉት በዞኑ ባሕልና ቱሪዝም መምሪያ የሆቴልና ቱሪዝም አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ብቃት ማረጋገጥ ቡድን መሪ አቶ ውብሸት ዋሲሁን የሚሳተፉት በዕድሜ ገፋ ያሉ ተፈጥሮን የሚያደንቁና የሚንከባከቡ ናቸው ብለዋል፡፡

በጋሞ ዞን በርካታ የቱሪስት መዳረሻዎች በመኖራቸው የሆቴል፣ የምግብ፣ መጠጥና የመኝታ አገልግሎት ሰጪ እና የመኪና አከራይ ማህበራት ከዘርፉ በሚያገኙት ገንዘብ ተጠቃሚ እየሆኑ ይገኛሉ እንደአቶ ውብሸት ገለጻ፡፡

ዘጋቢ፡ ገናናው ለማ