የአካል ጉዳተኞች ብንሆንም የአዕምሮ ጉዳተኞች አይደለንምና ለሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ተወካይ ሆነን በመመረጣችን ደስተኞች ነን

ሀዋሳ፡ ሰኔ 17/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሀገር ጉዳይ ለአንድ ወገን የሚገፋ አይደለምና ሁላችንም በተሰማራንበት ዘርፍ የድርሻችንን መወጣት አለብን ሲሉ በካፋ ዞን በተደረገው ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የተሳተፉ አካል ጉዳተኞች፣ ሀገር ሽማግሌዎችና የሃይማኖት ተወካዮች ገለጹ፡፡

አሁን ዘመኑ ከደረሰበት ሥልጣኔ አኳያ ሕዝብና መንግስት ተደማምጠው የሚሰሩበት ወቅት በመሆኑ የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ችግር ፈቺ እንደሚሆን በሕዝቡ ዘንድ ተስፋ የተጣለበት መሆኑም ተጠቁሟል፡፡

የአካል ጉዳተኞች ብንሆንም የአዕምሮ ጉዳተኞች አይደለንም የሚሉት የአካል ጉዳተኞች ተወካዮች ለሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ተወካይ ሆነው በመመረጣቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል፡፡

ምክክሩ ለሀገር ዕድገት ፋይዳው የላቀ በመሆኑ ቀጣይነት ያለውና ችግር ፈቺ መሆን እንዳለበት ተወካዮቹ መክረዋል፡፡

አካታች መሆኑ ደግሞ በየደረጃው የሚታዩትን ችግሮችን በመቅረፍ ለሀገር ሰላምና ለዲሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ አማራጩ ሰፊ እንደሆነም አመላክተዋል፡፡

ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግሮች እንዲፈቱ ትኩረት ማድረግ እንዳለበት የጠየቁት ከሀገር ሽማግሌዎች መካከል አቶ በየነ ዳከጉቾ የኮሚሽኑ ሂደት በሕዝቡ ዘንድ ተሰፋ የተጣለበት መሆኑንም አክለዋል፡፡

አሁን ዘመኑ ከደረሰበት ሥልጣኔ አኳያ ሕዝብና መንግስት ተደማምጠው የሚሰሩበት ወቅት መሆኑን ያመለከቱት አስተያየት ሰጪዎች ለጋራ ዕድገት ደግሞ የሀሳብ አንድነት ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ምክክር ከሌለ ሰላም የለምና ይሄው እንቅሰቃሴ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ያሉት ተወካዮች ከዚህ ቀደም ይደረጉ የነበሩት ምክክሮች ውጤት አልባ እንደነበሩም አንሰተዋል፡፡

ይሁን እንጂ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየታየ ያለው ለውጥ ተሰፋ ሰጪ መሆኑን የገለጹት የህይማኖት ተወካዮቹ የሀገር ጉዳይ ለአንድ ወገን የሚገፋ አይደለምና ሁላችንም በተሰማራንበት ዘርፍ የድርሻችንን መወጣት አለብን ብለዋል፡፡

ዘጋቢ፡ መለሰ ገብሬ – ከቦንጋ ጣቢያችን