ኮሚሽኑ የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎችን ወክለው ለሚሳተፉ ተወካዮች ያዘጋጀው መድረክ በሀዋሳ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል

ኮሚሽኑ የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎችን ወክለው ለሚሳተፉ ተወካዮች ያዘጋጀው መድረክ በሀዋሳ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል

ሀዋሳ: ሰኔ 01/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምክክር ኮሚሽን የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎችን ወክለው ለሚሳተፉ ተወካዮች ያዘጋጀው መድረክ በሀዋሳ ከተማ ሚሊንየም አዳራሽ እየተካሄደ ይገኛል::

በችግሮቻቸው ዙሪያ ያልተመካከሩ ሀገራት ዛሬ በቀውስ ውስጥ እንደሚገኙ የተናገሩት መድረኩን በንግግር የከፈቱት የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶ/ር ዮናስ አዳዬ ናቸው::

ለዘመናት ሲንከባለሉ በመጡ በርካታ ጉዳዮች ጊዜ ሰጥተን ባለመመካከራችን አሁን ለሚስተዋለው አለመግባባቶች ምክንያት ሆነዋል ያሉት ኮሚሽነሩ አሁን ግን በውይይት ለችግሮቻችን መፍትሔ የምናበጅበት ዕድል ተፈጥሯል ብለዋል::

የምክክር ሂደቱ ሁሉንም ያሳተፈ ሲሆን የሀይማኖት እና የባህል አባቶች፣ የፖለቲካ መሪዎች፣ ምሁራንና የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች በሀገራቸው ጉዳይ ላይ ከስሜት በፀዳ መንገድና ኢትዮጵያን በሚያሻግር መልኩ ሰፊ ምክክር ያደርጋሉ ብለዋል::

በዛሬው እለት ኮሚሽኑ የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎችን ወክለው ለሚሳተፉ ተወካዮች ባዘጋጀው መድረክ ላይ 3 ተወካዮች የሚመረጡ ይሆናል:: ከሚመረጡ ተወካዮች መካከል 2ቱ ዋና ተሳታፊ የሚሆኑ ሲሆን አንድ ሰው ደግሞ ተጠባባቂ ይሆናል ተብሏል::

ተወካዮቹ የሚመረጡት ለእውነት ባላቸው አቋም፣ በእውቀት፣ በማህበረሰብ ዘንድ ባላቸው ተአማኒነት ላይ ተመስርቶ ይሆናልም ነው ያሉት ኮሚሽነር ዶ/ር ዮናስ::

በሀዋሳ ከተማ በሁለት ማዕከላት ከተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች የተውጣጡ 3 ሺ 600 ዜጎች በውይይት መድረኩ እየተሳተፉ ይገኛሉ::

ዘጋቢ: ማሬ ቃጦ