በተለያዩ ዘርፎች የተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሰራ መሆኑን በካፋ ዞን የኦሞ ባንክ ጠሎ ቅርንጫፍ አስታወቀ

ሀዋሳ፡ ግንቦት 25/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) የኦሞ ባንክ አርሶ አደሩን እና በተለያዩ የንግድ የስራና በሌሎች ዘርፎች የተሰማሩ የህበረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሰራ መሆኑን በካፋ ዞን የኦሞ ባንክ ጠሎ ቅርንጫፍ አስታውቋል።

ባንኩ የአሰራር ስርዓቱን በማዘመን የደንበኞችን ቁጥር እያሳደገ እንደሚገኝም ተገልጿል።

በጠሎ ወረዳ የኦሞ ባንክ ስራ አስኪያጅ አቶ አሰጋኸኝ አበበ እንደገለጹት፤ ባንኩ ወደ ባንክ ደረጃ ከመሸጋገሩ በፊት ከ1998 ዓ.ም ጀምሮ ለአካባቢው ማህበረሰብ የብድር አገልግሎት በመስጠት የማህበረሰቡን የኢኮኖሚ ችግር ሲቀርፍ ቆይቷል።

በአሁን ወቅት ባንኩ ከብሄራዊ ባንክ በተሰጠው ፈቃድ መሰረት የአሰራር ስዓቱን በማሻሻል በባንክ በመደራጀት ከብድር ስርጭት በተጨማሪ ደንበኞች በባንኩ እንዲቆጥቡና ገንዘብ እንዲያንቀሳቅሱ ሰፊ ስራዎች እየተሰሩ ነው ብለዋል።

ባንኩ በተያዘው በጀት አመት ከ1መቶ ሚሊዮን ብር በላይ ማስጠቆብ መቻሉን የገለፁት ሀላፊው ከ6 ሚሊዮን ብር በላይ የብድር አገልግሎት መስጠት መቻሉንም ገልፀዋል።

በድለባ፣ በከተማ ግብርናና በተለያዩ የንግድ ስራዎች ለተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ባንኩ የብድር አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን የገለጹት አቶ አሰጋኸኝ ከዚህ ቀደም ከተቋሙ የብድር አገልግሎት ወስደው ያልመለሱ ማህበራት የወሰዱትን ብድር የማስመለስ ስራ በወረዳው ከተቋቋመው ግብረ-ሃይል ጋር በመሆን እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል።

በዚህም ከ10 ሚልዮን ብር በላይ ማስመለስ የተቻለ ሲሆን ይህ ስራ ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል ብለዋል አቶ አሰጋኸኝ።

የባንኩ ደንበኞች በበኩላቸው ባንኩ ባደረገው ማስተካካከያ መደሰታቸውን በመግለጽ ከቁጠባ በተጨማሪ ከባንኩ የብድር አገልግሎት በማግኘት ኑሯቸውን ለማሻሻል ማቀዳቸውን ነው የገለፁት።

ባንኩ ለአርሶ አደሮችና ለወጣቶች የፋይናንስ ምንጭ በመሆን ሥራ አጥነትን በመቀነስና ቁጠባን ባህል በማድረግ ረገድ ስኬታማ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል።

ዘጋቢ፡ ትዕግስቱ ጴጥሮስ – ከቦንጋ ጣቢያችን