የፈጠራ ስራ አዳዲስ ሀሳቦችንና እውቀቶችን በተግባር ላይ በማዋል ወደሚጨበጥ ኢኮኖሚ ለመቀየር ፋይዳው የጎላ መሆኑን በጉራጌ ዞን የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ጽህፈት ቤት አስታወቀ
ጽህፈት ቤቱ ከወልቂጤ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ጋር በመተባበር ከሐምሌ 1 እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2018 ዓ.ም በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ሲሰጥ የቆየውን የኮምፒዩተርና የተለያዩ የቴክኖሎጂ ሥልጠናዎች የማጠቃለያ መርሃ ግብር አካሂዷል።
የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሀምዱ ካሚል በመርሃ ግብሩ እንደገለፁት፤ በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በተለያዩ የስልጠና ዘርፎች ለ1 ሺህ 500 ሰልጣኞች ስልጠና ሲሰጥ ቆይቷል።
በዚህም አራቱ የኢትዮ-ኮደርስ ሰልጣኞች ስራዎቻቸውን ማቅረባቸውን ተናግረዋል።
ከነዚህም መካከል በዞኑ በግብርናው ዘርፍ በተለይ የእንሰት፣ የቡና እና የበቆሎ የምርታማነት ችግርን በዘላቂነት የሚቀርፍ ቴክኖሎጂ በመኖሩ ይህንንም ወደ ማህበረሰቡ ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን አመላክተዋል።
አቶ ሀምዱ አክለውም፤ የፐብሊክ ሰርቫንት ሰዓት አጠቃቀም ግልጽ የሆነ የመረጃ ሲስተም ማሽን በመጠቀም የመንግስት ሀብት ማዳን የሚያስችል ሌላኛው ቴክኖሎጂ መሆኑን አስረድተዋል።
በየተቋማቱ የሚገኙ የኤሌክትሮኒክ ዕቃዎችና ወንበሮችን በዘመናዊ መንገድ ለማስተዳደር አመቺ የሚያደርግ ሌላ የፈጠራ ማሽንም በሰልጣኞች መቅረቡን ጠቅሰዋል።
በክረምት በጎ ፈቃድ ተማሪዎች እምቅ የፈጠራ አቅማቸውን ወደ ተግባር በመቀየር ውጤት ማምጣት ተችሏል ብለዋል ኃላፊው።
ተማሪዎች በአእምሯቸው የሚመነጩ አዳዲስ ሀሳቦችንና እውቀቶችን በተግባር ላይ በማዋል ወደሚጨበጥ የኢኮኖሚ ጥቅም ወይም ወደ ገንዘብ በመቀየር የፈጠራ ስራዎቻቸውን ማሳደግ ይኖርባቸዋል ሲሉ አቶ ሀምዱ መክረዋል።
በቀጣይ የምርምር ማዕከላትን በሰፊው ገንብቶ በርካታ የፈጠራ ባለቤት ትውልድን ለመፍጠር የሚያስችሉ ስራዎች እንደሚሰሩ አመላክተው፤ የሚመለከታቸው አካላት ከግብዓት ድጋፍ ጀምሮ የቅንጅት ስራዎችን አጠናክረው ማስቀጠል እንደሚገባቸው አሳስበዋል።
በወልቂጤ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የጋርመንት የትምህርት ክፍል አሰልጣኝ አቶ መሮልማ ለገሰ፤ ኮሌጁ በተለያዩ የስልጠና ዘርፎች በየጊዜው ስልጠና እየሰጠ እንደሆነና ለውጤታማነቱ የሚመለከታቸው አካላት እገዛ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው ጠቁመዋል።
የስልጠና ስራዎቻቸውን ያቀረቡት ተማሪዎችም የፈጠራ ስራዎችን ለመስራት እና በዘርፉ ውጤታማ እንዲሆኑ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ጽህፈት ቤት ለሚያደርግላቸው ትብብር አመስግነዋል።
ሰልጣኞቹ በቀጣይ በዘርፉ ጠንክረው እንደሚሰሩ አንስተው፤ የግብዓት ውስንነቶች እንዳሉ ግን አልሸሸጉም።
ስለሆነም ችግሩን ለመቅረፍ የሚመለከታቸው አካላት እገዛ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ሲሉ ጠይቀዋል።
ዘጋቢ፡ ዝናሽ ሙሉጌታ – ከወልቂጤ ጣቢያችን

More Stories
የጌዴኦ ዞን ምክር ቤት 32ኛ የምክር ቤቶች የጋራ ምክክር ፎረም እያካሄደ ነው
የላስካ ከተማ ነዋሪዎችን የመሠረተ ልማት ጥያቄ ለመመለስ እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ
ለስድስት ሺህ ተማሪዎች ከ9 ሚሊየን ብር በላይ በማውጣት ድጋፍ ተደርጓል – የከምባታ ልማት ማህበር